Harambee radio 98.7

Harambee radio 98.7 [email protected]
ሀገራዊ እና አህጉራዊ ህብረታችንን ጠብቀን ወደተራራው ጫፍ ለመድረስ Arts & Entertainment

23/08/2023

በትግራይ ክልል ለሁለት ዓመታት ጡረታ ያልተከፈላቸው አረጋውያን በምግብ እጥረት እየሞቱ መሆኑ ተሰማ

በትግራይ ክልል ከሁለት ዓመታት በላይ የጡረታ ደመወዝ ያልተከፈላቸው አረጋውያን በምግብ እጥረት ለሕልፈተ ሕይወት እየተዳረጉ መሆኑን የክልሉ አረጋውያን ማኅበር ገልጿል፡፡
ከዓመታት በፊት ጡረታ የወጡ አረጋውያን ብዛት 75 ሺሕ ሲሆን፤ አሁን ላይ ቁጥራቸው ወደ 100 ሺሕ የሚጠጉ መሆናቸውን የክልሉ አረጋውያን ማኅበር ያሳወቀ ሲሆን፤ ከሁለት ዓመታት በላይ የጡረታ ደመወዝ ያልተከፈላቸው አረጋውያንም በምግብ እጥረት እየሞቱ መሆኑን የማኅበሩ ሊቀመንብር አቶ አርዓያ ገሠሠ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
የሰባት ወር የሚሆን ተብሎ የጡረታ ደመወዝ ቢለቀቅላቸውም፤ የተወሰኑ ሰዎች ሲያገኙ አብዛኛዎቹ ገና በመጠባበቅ ላይ እንዳሉም ሊቀመንበሩ አክለዋል፡፡
አቶ አርዓያ ለሁለት ዓመታት የጡረታ ደመወዝ አልተከፈላቸውም ከተባሉት አረጋውያን መካከል በምግብ እጥረት የሞቱት ምን ያህል እንደሆኑ አለመታወቁን ጠቅሰው፤ የፌዴራሉ መንግሥት ይህን ችግር እንዲቀርፍ ጠይቀዋል፡፡
ከጥር ወር 2015 ዓ.ም. ወዲህ በክልሉ ከ1 ሺህ 3 መቶ በላይ ሰዎች በረሃብ መሞታቸውን፣ የክልሉ አደጋ ሥጋት አመራር ኮሚሽን፣ ለፌዴራልና ለዓለም አቀፍ ሰብዓዊ ድርጅቶች ዓርብ ሐምሌ 14 ቀን 2015 ዓ.ም. ባቀረበው ሪፖርት አስታውቆ ነበር፡፡
በስርቆት ምክንያት የዕርዳታ ድጋፍ ካቆመ ጊዜ ወዲህ ግን ሕይወታቸው በጥር ወር አልፏል ከተባለው ቁጥር በላይ ከፍ ማለቱን፣ የክልሉ አደጋ ሥጋት ኮሚሽን ለተለያዩ የሚዲያ አውታሮች ይፋ አድርጎ ነበር፡፡
ኮሚሽኑ የሟቾቹን ቁጥር ይፋ ያደረገው፣ በማዕከላዊ ዞን 22 ወረዳዎች፣ በደቡብ ትግራይ ዞን በስድስት ወረዳዎች፣ እንዲሁም በምዕራብ ትግራይ መሆኑም ተነግሯል፡

23/08/2023

በምስራቅ ወለጋ ኪራሙ ወረዳ ሰዎች መገደላቸውና፣ ከብቶች መዘረፋቸው ተሰማ

በምስራቅ ወለጋ ኪረሙ ወረዳ ውስጥ እሁድ እለት ታጣቂዎች ባደረሱት ጥቃት ስድስት ሰዎች እንደተገደሉ እና በንብረትም ላይ ጉዳት መድረሱ ተገልጿል። የአካባቢዉ ነዋሪዎች እንዳሉት ታጣቂዎቹ በሁለት ቀበሌዎች ላይ ዘምተዉ ሰዉ ከመግደልና ንብረት ከማጥፋታቸዉ በተጨማሪ የቁም እንስሳትንም ዘርፈዋል ብለዋል፡፡
የወረዳው አስተዳደር በበኩሉ በሁለቱ ቀበሌዎች ውስጥ በደረሰው ጥቃት የሰው ህይወት ማለፉን አረጋግጧል፡ በምስራቅ ወለጋ ኪረሙ ወረዳ እና በሆሮ ጉዱሩ ወለጋ አሙሩ የተባለ ወረዳ ውስጥ በተለያዩ ጊዜ ለሚደርሱ ጥቃቶች በፋኖ እና በሸኔ ስም የሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎችን ተጠያቂ እነደሆኑ ነዋሪው ይገልፃል።
የኪረሙ ወረዳ ኮሙኒኬሽን ጉዳዩች ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ጅረኛ ሂርጳ በወረዳው ሁለት ቀበሌ ውስጥ ሰሞኑን ከአማራ ክልል የተሻገሩ የታጠቁ ሀይሎች ጉዳት ማድረሳቸውን ስድስት ሰዎች መግደላቸውን አመልክተዋል፡፡
በምስራቅ ወለጋ ኪረሙ ወረዳ 10 ከሚደርሱት ቀበሌዎች ውስጥ ከዚህ ቀደም በነበረው የጸጥታ ችግር ምክንያት በወረዳው 52ሺ በ8 መቶ 22 ሰዎች ተፈናቅለው እንደሚገኙም የተገለፀ ሲሆን በጉዳዩ ላይ የምስራቅ ወለጋ ዞን ምንም አለማለቱን የዘገበው ዶቼቨለ ነው፡፡

21/08/2023

ኡጋንዳ ያለዓለም ባንክ ድጋፍ ለመቀጠል ማቀዷ ተገለጸ

የተመሳሳይ ጸታ ጋብቻን የሚከለክል ህግ ማጽደቋን ተከትሎ ብድር እና ሌሎች ድጋፎችን የተከለከለችው ኡጋንዳ የአለም ባንክ ድጋፍ ለመቀጠል እቅድ ማዘጋጀቷ ተሰምቷል።
የዓለም ባንክ ለኡጋንዳ አዲስ ብድር እንደማይሰጥ ማስታወቁን፤ ኡጋንዳም ያለ አለም ባንክ ድጋፍ መኖር እንደምትችል ማሳወቋ የሚታወስ ሲሆን ይህንን ተከትሎም ኡጋንዳ ያለአለም ባንክ ድጋፍ ህይወትን ለመቀጠል የሚያስችል እቅዶችን መንደፏን የኡጋንዳው ሞኒተር ጋዜጣ በድረ ገጹ አስንብቧል።
የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻ የሚከለክል ህግ ማጽደቋን ተከትሎ በምዕራባዊያን ሀገራት ስትወገዝ የቆየችው ምስራቅ አፍሪካዊቷ ኡጋንዳ አዳዲስ የገንዘብ ምንጮችን እያፈላለገች ነው የተባለ ሲሆን፤ ከእነዚህም ውስጥ እንደኛው በአፍሪካ ውስጥ ተጽእኖዋ እያደገ ከመጣው ቻይና ጋር ተቀራሮቦ መስራት ሲሆን ከህንድ ጋር ያላትን ግንኙነት ማሳደግንም እንደ አማራጭ የያዘችው ኡጋንዳ፤ የዩሮ ቦንዶችን ማዘጋጀት እና ለጨረታ በማቅረብ ገንዘብ ለማግኘት መወጠኗም ተነግሯል።
ሌላኛው ኡጋንዳ እንደ አማራጭ የያዘችው መፍትሄ በሀገር ውስጥ የገንዘብ አጠቃቀም ላይ ማስተካከያዎችን መውሰድ ሲሆን፤ በዚህም ሀገሪቱ ለመንግስት ባለስልጣናት በውድ ብር ሊገዙ የነበሩ የመኪናዎችን ግዢዎችን መሰረዟን እና ከዚህ በኋላ አዳዲስ የመኪና ግዢ እንደማይኖርም የሀገሪቱ ገንዘብ ሚኒስቴር አስታውቋል።
ምዕራባዊያን አፍሪካን ዝቅ አድርገው መመልከት እና ጫና ማሳደር ይፈልጋሉ፣ እኛ ችግራችንን እንዴት መፍታት እንዳለብን እናውቃለን፣ እነሱም የእኛ ችግሮቻችን ናቸው ሲሉ ፕሮዝዳንት ሙሴቪኒ መናገራቸው የሚታወስ ነው።
ፕሬዝዳንቱ አክለውም ኡጋንዳ ከዓለም ባንክ ጋር ያለባትን ችግር ለመፍታት የሚቻል ከሆነ ውይይት ለማድረግ ትቀጥላለች ማለታቸውም አይዘነጋም።

21/08/2023

በፀጥታ ችግር ምክንያት የአምስት መስኖ ፕሮጀክቶች ግንባታ መቆሙ ተገለጸ

የፀጥታ ችግር በሚስተዋልባቸው በኦሮሚያ፣ አማራና ትግራይ ክልሎች የሚገኙ ፕሮጀክቶች ግንባታቸው መቆሙን የመስኖና ቆላማ አካባቢ ሚኒስቴር ገለፀ፡፡
ሚኒስቴሩ ከያዛቸው 17 የግድብ ፕሮጀክቶች መካከል ወደ አምስት የሚሆኑት ፕሮጅክቶች በፀጥታ ችግር የቆሙ መሆናቸውን የሚኒስቴሩ የሕዝብ ግንኙነትና የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ብዙነህ ቶልቻ ገልጸዋል፡፡
ከለውጡ በኋላ ተጀምረው በተለያዩ የፀጥታ ችግሮች ግንባታቸው የቆሙ አሉ ያሉት አቶ ብዙነህ የላይኛው ጉደር ግድብና የመስኖ ልማት ፕሮጀክት በሚሠራበት አካባቢ በሚስተዋለው የፀጥታ ችግር ከቆሙት ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ መሆኑን አስረድተዋል፡፡ በትግራይ ክልል የሚገኘው የካዛ ግድብና መስኖ ልማት ሎት ግንባታ በፀጥታ ችግር እንደቆመም አክለዋል፡፡
በተጨማሪ በአማራ ክልል የሚገኘው የመገጭ ግድብ ፕሮጀክት ለ18 ዓመት መጓተቱን የገለጹት አቶ ብዙነህ፣ በባሌ በምሥራቅ ባሌ ዞን የሚገኘው ጨልጨል የመስኖ ፕሮጀክት፣ በኦሮሚያ ክልል የሚገኘው አንገር ፕሮጀክት ውል ከተገባ በኋላ በፀጥታ ችግር ማጠናቀቅ አለመቻሉን ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል ከ85 ቢሊዮን ብር በላይ በጀት ፈሰስ የጠየቁ 17 የመስኖ ፕሮጀክቶች መካከል የተጓተቱ እንዳሉም የገለጹ ሲሆን በአጠቃላይ ሚኒስቴሩ 27 የግድብ ፕሮጀክቶች እንዳሉት፣ ከ27ቱ ፕሮጀክቶች መካከል 17 የሚሆኑት ከ85 ቢሊዮን ብር በላይ ፈሰስ እንደተደረገባቸው፣ ከ27ቱ የአምስቱን ግድቦችን ግንባታ ለማስጀመር ገና የኮንትራክተር ሥራ ተቋራጭ ሒደት ላይ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ፕሮጀክቶቹ እንዳይሳኩ የአቅም ችግር አለ ያሉት ሃላፊው ከማስፈጸም አንጻር፣ የፋይናንስ አቅም ማነስ፣ የመስኖ ፕሮጀክቶችን የሚገነቡ አማካሪ ድርጅቶችና የሥራ ተቋራጮች ግንባታ በሚያካሂዱበት ጊዜ የተለያዩ የማሽነሪ አቅም ችግር ስለሚኖር በኪራይ ስለሚሠሩ ኪራይም በሚፈለገው ልክ አቅርቦት ባለመኖሩ ፕሮጀክት ተሰጥተው በገቡት ውል መሠረት ሠርተው ማስረከብ አልቻሉም ብለዋል፡፡

21/08/2023

ኢሀፓ የሕዝብን መብት በጠመንጃ ማፈን ጥፋትን እንጂ ሰላምን አያመጣም ሲል ገለፀ

የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ ኢሀፓ የአማራ ክልል ወቅታዊ ሁኔታን በተመለከተ ባወጣው መግለጫ የሕዝብን መብት በጠመንጃ ማፈን ጥፋትን እንጂ ሰላምን አያመጣም ሲል ገልጿል፡፡
ለሀራምቤ ሬዲዮ በላከው መግለጫም በክልሉ ውስጥ በሚደረገው ሕዝባዊ ትግል ሕይወታቸውን ላጡ ኢትዮጵያውያን ሁሉ የተሰማውን ጥልቅ ሐዘን በመግለፅ ለቤተሰቦቻቸውም መፅናናቱን እንመኛለን ብሏል፡፡
ፓርቲው በብሄር ብሄረሰብ ስሪት የተገነባ አገዛዝ ለጊዜው ኢኮኖሚውን ከፍ ቢያደርግም የፀና እና የተረጋጋ ሰለም የሰፈነበት ሀገር ለመመስረት ግን አያስችልም ያለ ሲሆን፤ የአማራ ህዝብ ከአሁን ቀደም በነበረው አገዛዝ እና በአሁንም በመንግስት የጨቋኝነት ፍረጃ እየተካሄደበት እልፍ መከራዎችን እያሳለፈ ይገኛል ብሏል፡፡
ፓርቲው መንግሥት እመራበታለሁ የሚለው ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 14፣ “ማንኛውም ሰው ሰብዓዊ በመሆኑ የማይደፈርና የማይገሰስ፣ በሕይወት የመኖር፣ የአካልና ደኅንነት መብት አለው” የሚለውን ጥሶ የዜጎችን መብት ማፈን፤ የመከሰስ መብታቸው በሕግ የተከበረ መሆኑ እየታወቀ የፓርላማ አባላትን ከቤታቸው ወስዶ ማሠር፣ ሕገ=መንግሥታዊ ጥሰት ከመሆኑ በላይ ችግሩን ያባብሰዋል እንጂ መፍትሄ አያመጣም ብሏል በመግለጫው፡፡
በመሆኑም ከችግሩ ውስብስብነት አንጻር በአግባቡ ካልተፈታ በሀገር ህልውና ላይ ሊያመጣ የሚችለውን አደጋ በማገናዘብ መንግሥት የሚከተልቱን እርምጃዎች ያለመንም ቅድመ ሁኔታዎች ተግባራዊ እንዲያደርግ ሲል ፓርቲው አጥብቆ የጠየቀ ሲሆን፤ ከቅድመ ሁኔታዎች ውስጥም የመከላከያ ሠራዊትን ከአማራ ክልል በአስቸኳይ ማስወጣት እና ጊዜያዊ አዋጁን መሰረዝ የሚሉት ይገኙበታል፡፡
በአዲስ አበባና በመላው ኢትዮጵያ በማንነታቸውና በፖለቲካ እምነታቸው የታሠሩ ዜጎችን በአስቸኳይ እንዲፈቱ በአማራ ሕዝብ ላይ ለዘመናት የተፈጸሙት የፖለቲካ፣ የኤኮኖሚ፣ የማኅበራዊና የሥነልቦናዊ ጭቆናዎች በዓለምአቀፋዊና ሃገራዊ ነፃ ተቋማት ተጠንተው ተገቢው ፍትኅ አንዲሰጥ እንዲያደርጉ ሲልም አሳስቧል፡፡
የአማራ ሕዝብ ያነሳቸው የኅልውና ጥያቄዎች፣ ደህንነቱና ሙሉ መብቱ እስኪረጋገጡ ድረስ ትጥቅ የማስፈታትን ጉዳይ በይደር እንዲያዝ እና የወልቃይት፣ የጠለምት፣ የጠገዴ፣ የራያ አስተዳደሮች አሁን ባሉበት እንዲቆዩ ማድረግና ሁኔታው ሲፈቅድ በውይይት እንዲፈቱ ማድረግ እንደሚገባ አስታውቋል፣
ለተፈናቀሉ ወገኖች ሀገራዊና ዓለማቀፋዊ ያልተገደበ ዕርዳታ እንዲደረግ፣ የመልሶ ማቋቋም ተግባር እንዲጀመር የተገደቡ የዴሞክራሲ መብቶች ያለምነም ቅድመ ሁኔታዎች መልቀቅ፣ ያለ ፍርድ ቤት ትዕዛዝ የሚከናወኑ እሥራት፣ አፈሳና አፈና በአስቸኳይ ማቆም ይገባል ብሏል፡፡ በመገናኛ ብዙሃን ላይ የሚደረገው አፈናና በጋዜጠኞች ላይ የሚደረገው እሥራት በአስቸኳይ ማቆም እና የጎሳ ፖለቲካ በሕግ እንዲታገድ አጥብቀን እንጠይቃለን ሲል በመግለጫው አስታውቋል፡፡

21/08/2023

በአዲስ አበባ በሞተር ብስክሌት ተሽከርካሪዎች ላይ ተጥሎ የነበረው እገዳ መነሳቱ ተሰምቷል

ከዚህ ቀደም በአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ ለምን እንደሆነ ባልታወቀ ምክንያት በሞተር ብስክሌት ተሽከርካሪዎች ላይ ተጥሎ የነበረው እገዳ መነሳቱ ተነገሯል፡፡
በአዲስ አበባ የሚገኙ የሞተር ብስክሌት አሽከርካሪዎችና ባለንብረቶች በሙሉ ከዛሬ ጀምሮ ከአሽከርካሪው ውጪ ሌላ ተጨማሪ ተሳፋሪ ሳይጨምሩ የሞተር ብስክሌት ማሽከርከር እንደሚቻል የአዲስ አበባ ትራንስፖርት ቢሮ አሳውቋል፡፡
ከተፈቀደው የሰው መጫን አቅም በላይ በሚጭኑ ማህበራትና አሽከርካሪዎች ላይ ቢሮው ጥብቅ እርምጃ እንደሚወስድ ገልጿል።
አሽከርካሪዎችም ለትራፊክ አደጋ መንስኤ ከሆኑ ከፍጥነት በላይ ማሽከርከር፣ የራስ ቆብ መከለያ (ሄልሜት) አለመጠቀም፣ ከወንጀል ድርጊት በመራቅና ወንጀል የሚፈጽሙ ሲያጋጥሙም ለጸጥታ አካላት ጥቆማ እንዲሰጡ ሲልም ቢሮው አሳስቧል።

21/08/2023

ለደረሰው ውድመት መልሶ ግንባታ ኢትዮጵያ የዓለማቀፍ ተቋማት ድጋፍ እንደሚያስፈልጋት ተገለፀ

በሰሜኑ ጦርነት በአገሪቱ ላይ ለደረሰው ውድመት መልሶ ግንባታ ኢትዮጵያ የዓለማቀፍ ተቋማትን ድጋፍ በጽኑ ትፈልጋለች በማለት የኢትዮጵያ ገንዘብ ሚንስትር አቶ አሕመድ ሽዴ ተናግረዋል።
አገሪቱ ለመልሶ ግንባታም በቀጣዮቹ አምስት ዓመታት 20 ቢሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልጋት ሚንስትሩ መናገራቸው የተገለፀ ሲሆን መንግሥት ከዓለማቀፉ የገንዘብ ድርጅት ጋር የጀመረው የብድር ድርድር ከፍተኛ ደረጃ መድረሱም ተገልጽዋል።
የፌደራሉና ክልል መንግሥታት ከበጀታቸው ከፊሉን ለመልሶ ግንባታ እንደሚመድቡ የገለፁት አሕመድ፣ ከሁሉም በላይ ግን የዓለም ባንክ ድጋፍ ያስፈልገናል ማለታቸውም ተሰምቷል።

21/08/2023

ከመጠለያ ውጪ ናቸው የተባሉ ከ60 ሺሕ በላይ የጋሞ ተፈናቃዮችን መንግሥት እንዲያቋቁም የጋሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ጋዴፓ) ጥያቄ አቀረበ

ከሸገር ከተማና ዙሪያ ቤት የፈረሰባቸው ከ60 ሺሕ በላይ የጋሞ ዞን ማኅበረሰቦች ወደ ዞኑ ተመልሰው በዞኑ በሁሉም ከተሞች እንዲሚገኙ እና የመሬት ጥበት ስላለ እስካሁን መቋቋም እንዳልቻሉና መጠለያ እንዳላገኙ ፓርቲው አስታውቋል፡፡
የተፈናቀሉት ሰዎች አኗኗራቸው ሕገወጥ ነው ከተባለ ሕገወጥነትን ወደ ሕጋዊነት ለማዞር መንግሥት ዕርምጃዎችን ሊወስድ ይችላል ነገር ግን ዜጎችን ሙሉ ለሙሉ አውጥቶ መጣል ኃላፊነት የተሞላበት የመንግሥት አሠራር አይደለም፡፡ የማቋቋም ኃላፊነቱን መንግሥት እንዲወስድ በተደጋጋሚ እየጮህን ነበር፣ አንድም ተግባራዊ የተደረገ ነገር የለም መንግሥት ቤት ፈርሶባቸው የተፈናቀሉ ሰዎችን መጠለያ የማግኘት መብት በማስከበር የማቋቋም ኃላፊነቱን እንዲወጣ በማለት የፓርቲው ሊቀመንበር አቶ ዳሮት ጉምአ አሳስበዋል፡፡
ከአዲስ አበባ ወደ ጋሞ ዞን ተፈናቅለው የሠፈሩት ሰዎች ከቤተሰቦቻቸው ጋር በአጠቃላይ ብዛታቸው ከ60,000 እስከ 70,000 እንደሚሆኑና ተፈናቃዮቹ የሚገኙት በጋሞ በሁሉም ወረዳዎች እንደሆነ የፓርቲው ሊቀመንበር ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ከአገር ውስጥ ተፈናቃይ ተወካዮች ጋር በአዲስ አበባ ከተማ ከነሐሴ 7 እስከ 8 ቀን 2015 ዓ.ም. አደረኩት ባለው ውይይት፣ ልዩ ድጋፍ ለሚሹ የአገር ውስጥ ተፈናቃዮች የሚደረጉ የሰብዓዊ፣ የፀጥታና የደኅንነት፣ የተሳትፎና የመንቀሳቀስ መብቶች እየተከበሩላቸው እንዳልሆነ ማስታወቁ የሚታወስ ነው፡፡

21/08/2023

የሳዉዲ የጸጥታ ሃይሎች በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያዉያን ስደተኞችን መግደላቸው ተሰማ

የሳውዲ የጸጥታ ሃይሎች በመቶዎች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ስደተኞች እና ጥገኝነት ጠያቂዎች በየመን ድምበር ሃገሪቱን ለማቋረጥ ሲሞክሩ መግደላቸውን ሂውማን ራይትስ ዎች ገልጿል፡፡
መቀመጫውን ኒው ዮርክ ያደረገው የሰብአዊ መብት ተሟጋች ድርጅት ባወጣው ዘገባ ከምስክሮች ጋር በተደረገ ቃለ ምልልስ እና በፎቶዎች፣ ቪዲዮዎች እና የሳተላይት ምስሎች ከ2021 ወዲህ ያለዉን ጥናት መሰረት በማድረግ ስልታዊ ነው ያለውን ግድያ ዘርዝሯል።
የሳዉዲ አረቢያ መንግስት የፖሊሲው አካል አድርጎ ስደተኞችን የመግደል ተግባር የሚፈጽም ከሆነ እነኚህ ግድያዎች በሰው ልጆች ላይ የሚደረግ ወንጀል ናቸው ሲል ሂውማን ራይትስ ዎች ጠቅሷል፡፡
የሳዑዲ ድንበር ጠባቂዎችን ምናልባትም ልዩ ክፍሎችን ጨምሮ በቅርብ ዓመታት ውስጥ "በመቶዎች ከዚህም ሲያልፍ በሺዎች የሚቆጠሩ" ኢትዮጵያውያንን ሲገድሉ በሕይወት የተረፉትን እና እስረኞችን ለእንግልት፣ አስገድዶ መድፈር እና ሌሎች ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶች ተፈጽመዋል ሲል ከሷል።
የሳዑዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አስተያየት እንዲሰጥ ለቀረበለት ጥያቄ ምላሽ አለመስጠቱ የተገልጸ ሲሆን ሂዩማን ራይትስ ዎች በተጨማሪም ለበርካታ የሳዑዲ ተቋማት የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስቴር እና የሰብአዊ መብት ኮሚሽንን ጨምሮ መልክቱን ቢያጋራም ምንም ምላሽ አላገኝም ሲል ዋሺንግተን ፖስት ዘግቧል፡፡
ከ750 ሺህ የሚጠጉ ኢትዮጵያውያን በሳውዲ አረቢያ የሚኖሩ ሲሆን አብዛኞቹ "በመደበኛው መንገድ" ወደ ሃገሪቱ እንደደረሱ የአለም አቀፍ የስደኞች ድርጅት አስታውቋል።
በሳውዲ አረቢያ ድንበር አቅራቢያ የሚገኘውን ሰሜናዊ የሳዳ ግዛትን የሚቆጣጠረው የሳውዲ አረቢያ እና የየመን ሁቲ ንቅናቄ ስደተኞችን በጥሩ ሁኔታ ባለመያዝ ለጥቃት በማጋለጥ ተከሷል ሲል ሂዩማን ራይትስ ዎች ገልጿል።

17/08/2023

የጋሞ ዞን በክላስተር አደረጃጀት ዉስጥ መካተቱን እንደማይቀበል ተገለጸ

የጋሞ ዞን በክላስተር የክልል አደረጃጀት ዉስጥ መካተቱን እንደማይቀበለው የጋሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ(ጋዴፓ) አስተወቀ፡፡
የጋሞ ህዝብ ጥያቄ በክላስተር የመደራጀት አይደለም ያለው ፓርቲዉ፤ ህዝቡ ለረዥም ጊዜ ሲጠይቅ የቆየው ራሱን በራሱ የማስተዳደርና በክልል የመደራጀት ህገመንግስታዊ መብቱ እንዲከበርለት ነው ብሏል፡፡
አዲሱን የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል የመሰረቱት የጌዲኦ፣ የወላይታ፣ የጋሞ፣ ጎፋ፣ የኮንሶ፣ የደቡብ ኦሞ ዞኖች እንዲሁም የቡርጂ፣ የአማሮ፣ የደራሼ፣ የባስኬቶ እና የአሌ ልዩ ወረዳዎች መሆናቸው ይታወቃል፡፡
ይሁን እንጂ የጋሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ፣ የጋሞ ዞን በክላስተር የክልል አደረጃጀት ውስጥ መካተቱን እንደማይቀበለው በመግለጽ የጋሞ ህዝብ ጥያቄ በክላስተር ልደራጅ የሚል አይደለም ያለው ፓርቲው፤ ህዝቡ ራስን በራስ የማስተዳደር ህገ-መንግሥታዊ መብቱ እንዲከበርለት ነው የጠየቀው ብሏል፡፡
”የጋሞ ዞን ህዝብ ጥያቄ ከማዕከልነት ጋር የተያያዘ ወይም የከተማ አመዳደብ ኢ-ፍትሃዊነት ጉዳይ አይደለም“ ያሉት የጋሞ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ አቶ ቡንካሾ ሀንጌ፤ የህዝቡ ጥያቄ የክልልነትና ራስን በራስ የማስተዳደር ህገ-መንግስታዊ ጥያቄ ነው ብለዋል፡፡
“የጋሞ ህዝብ በፊት ሐዋሳ መጥቶ ነበር አገልግሎቶችን የሚያገኘው፤ በአዲሱ አደረጃጀት ግን አገልግሎት ለማግኘት ዲላ ድረስ መምጣት አለበት፤በዚያ ላይ ከአንድ ማዕከል አገልግሎቶችን ማግኘት የማይቻልበት ሁኔታ ተፈጥሯል“ ሲሉ አስረድተዋል፡፡

17/08/2023

ምሥራቅ ጉራጌ የተባለ አዲስ ዞን እንዲቋቋም የአካባቢው ተወላጆች ጠየቁ

በጉራጌ ዞን አራት ወረዳዎችና ሦስት የከተማ አስተዳደር ነዋሪ ተወካዮች ምሥራቅ ጉራጌ ዞን “የተባለ አዲስ የዞን አስተዳደር እንዲዋቀርላቸው ሀዋሳ ከተማ በሚገኘው የደቡብ ክልል ምክር ቤት ፊት ለፊት በመሰባሰብ ባካሄዱት ሠላማዊ ሰልፍ ጠይቀዋል፡፡

ሠልፈኞቹ የያዟቸው መፈክሮችም እስካሁን ባለዉ ጉራጌ ዞን ሥር ከሚገኙ የአስተዳደር መዋቅሮች መካከል አራት የወረዳ እና ሦስት የከተማ አስተዳደሮች “ ምሥራቅ ጉራጌ ዞን “ የተባለ አዲስ የዞን አስተዳደር እንዲዋቀር የሚጠይቁ ናቸው ፡፡ “የምሥራቅ ጉራጌ ዞን “ በሚል በአዲስ ዞን እንዲዋቀሩ ሠልፈኞቹ ጥያቄ ያቀረቡባቸው የመስቃን ፣ የምሥራቅ መስቃን ፣ የሶዶ ፣ የቡኢ ወረዳዎችና እንዲሁም የቡታጅራ ፣ የሶዶ እና የኢኒሴኖ ከተማ አስተዳደሮች ናቸው ተብሏል፡፡

17/08/2023

የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን ሊቀመምበር ሙሳ ፋኪ በአማራ ክልል ያለዉን ግጭት እየተከታተሉ እንደሆነ አስታወቁ

የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ በአማራ ክልል እየተካሄደ የሚገኘውን "ወታደራዊ ግጭት" እየተከታተሉት መኾኑን ባወጡት መግለጫ አስታውቀዋል።
ፋኪ፣ በክልሉ ግጭት ውስጥ የገቡ ወገኖች፣ "ግጭቱን ባስቸኳይ እንዲያቆሙ"፣ "የሰላማዊ ሰዎችን ደኅንነት እንዲጠብቁ" እና "ችግሩን ለመፍታት ንግግር እንዲጀምሩ" ጠይቀዋል።
አፍሪካ ኅብረት ለኢትዮጵያ ሕገመንግሥታዊ ሥርዓት፣ ለግዛት አንድነቷና ለሉዓላዊነቷ ያለውን ቀናዒነት የገለጡት ፋኪ፣ ኅብረቱ በአገሪቱ ሰላምና መረጋጋት ለማስፈን፣ በይነ-ኢትዮጵያዊያን ለኾነ የሰላም ጥረት ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መኾኑን አረጋግጠዋል።

17/08/2023

በአዲስ አበባ ከተማ “በትምህርት ቤቶች” እና “በተለያዩ ቦታዎች” የታሰሩ ሰዎች መኖራቸዉ ተገለጸ የሰላም ሚኒስቴር አስታወቀ

በአማራ ክልል ከተከሰተው የጸጥታ ችግር ጋር በተያያዘ በአዲስ አበባ ከተማ “በትምህርት ቤቶች” እና “በተለያዩ ቦታዎች” የታሰሩ ሰዎች መኖራቸውን የሰላም ሚኒስትሩ አቶ ብናልፍ አንዷለም ተናግረዋል። በፖሊስ ቁጥጥር ስር መዋላቸው በይፋ ከተገለጹ ግለሰቦች ውጭ ያሉ እስሮች የተፈጸሙት፤ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር እንጂ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ መምሪያ ዕዝ (ኮማንድ ፖስት) አለመሆኑንም ሚኒስትሩ ገልጸዋል።
የሰላም ሚኒስትሩ በአዲስ አበባ የታሰሩ ሰዎችን በተመለከተ ማረጋገጫ የሰጡት፤ ከፖለቲካ ፓርቲዎች ተወካዮች ጋር ሰኞ ነሐሴ 8፤ 2015 ባደረጉት ውይይት ላይ ይህንኑ አስመልክቶ ለተነሱላቸው ጥያቄ በሰጡት መልስ ነው።
በአቶ ብናልፍ እና የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መላኩ አለበል የተካሄደው ስብሰባ ፤ በአማራ ክልል የተከሰተውን የጸጥታ ችግር አስመልክቶ ለፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮቹ ገለጻ ለማድረግ እንደነበረ ታውቋል።
ሶስት ሰዓት ከ40 ደቂቃ ገደማ በፈጀው በዚህ ስብሰባ ላይ፤ ሁለቱ ሚኒስትሮች ያቀረቡትን ገለጻ ተከትሎ ከፖለቲካ ፓርቲ ተወካዮች ሀሳብ እና ጥያቄዎች ተሰንዝረዋል። አብዛኛዎቹ ተሳታፊዎች በአማራ ክልል ለተከሰተው ግጭት መንግስትን ጥፋተኛ ያደርጉ ሲሆን፤ በዚህም መንግስት በክልሉ ላለው ችግር አስቀድሞ መፍትሄ ከመስጠት ይልቅ “ጉዳዩን በኃይል ለመፍታት ሞክሯል” ሲሉም ወቅሰዋል ነዉ።

17/08/2023

በትግራይ ክልል የሰባዊ ድጋፍ መቋረጡን ተከትሎ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች በረሃብ ህይወታቸው እንዳለፈ ተሰማ

በትግራይ ክልል ዓለም አቀፍ ድጋፍ ሰጪ ድርጅቶች አስቸካይ ሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት ማቋረጣቸውን ተከትሎ፤ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ሰዎች በረሃብ ምክንያት ህይዋታቸው ማለፉ ተሰምቷል፡፡
በዚህም በሦስት ዞኖች ብቻ 1 ሺሕ 411 ሰዎች በረሃብ ምክንያት ሕይወታቸው ማለፉን የክልሉ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን አስታወቋል፡፡
የትግራይ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶክተር ገብረሕይወት ገብረ እግዛብሔር ለድምፂ ወያነ እንደገለጹት፤ በትግራይ ያለው የረሃብ አደጋ አሳሳቢ እና እጅግ አስፈሪ ደረጃ ላይ ደርሷል ብለዋል፡፡
ወቅቱ የክረምት ወራት ከመሆኑ ጋር ተያይዞም ብርድና ዝናብ ተጨምሮ ሁኔታው እጅግ አደገኛ እንዲሆን ማድረጉን የገለፁት ዶ/ር ገብረሕይወት፤ ሰብአዊ እርዳታ መቋረጡን ተከትሎ በሦስት ዞኖች ብቻ 1 ሺሕ 411 ሰዎች በረሃብ ምክንያት ሕይወታቸው ማለፉን ተናግረዋል።
በተለይም በጦርነቱ ምክንያት ከአካባቢያቸው ተፈናቅለው የመጡት ከ2 ነጥብ 6 ሚልዮን በላይ ተፈናቃዮች እጅግ በጣም በሚያሳዝን ሁኔታ ውስጥ መውደቃቸውን በመግለጽ፤ በየቀኑ የበርካታ ተፈናቃዮች ሕይወታቸው እያለፈ እንደሚገኝም ገልጸዋል፡፡
የዓለም የምግብ ፕሮግራም በኢትዮጵያ ላለፉት 5 ወራት አቋርጦት የነበረውን የምግብ እርዳታ ስርጭት፤ የእርዳታው ተጠቃሚዎች በምን መልኩ እንደሚመረጡ ከፍተኛ ቁጥጥር ካደረገ በኋላ በያዝነው ሐምሌ ወር ለመጀመር እቅድ መያዙን ማስታወቁ መዘገቡ ይታወሳል፡፡

14/08/2023

ባልደራስ ለእውነተኛ ዲሞክራሲ ፓርቲ በታሰሩበት አባላቶቹ ጉዳይ ላይ ለምርጫ ቦርድ እና ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ደብዳቤዎችን የፃፈ ሲሆን አጋጣሚዎችን በመጠቀም አባላቶቸ ላይ ያልተገባ ጥቃት እየደረሰ ነው ብሏል።

ከሰሞኑም በአማራ ክልል ላይ የተፈጠረውን ሁኔታ ምክንያት በማድረግ ኣባላቶቼ እየታሰሩና እየደተሳደዱ ይገኛሉ ሲል አክሏል።
በደብዳቤውመ ወይዘሮ ቅድስት በቀለ፣ ወጣት አዶኒያስ ገሰሰ፣ አቶ ሳሙኤል ዲሚትሪ፣ ወጣት ሰለሞን አላምኔ የተባሉ አራት አባሎቹም በመንግስት የፀጥታ ሀይሎች ታፍነው እንደተወሰዱበት ገልጿል።
በመሆኑም ፓርቲያችን ይህንን ችግር በነሐሴ 5/2015 ዓ.ም በተፃፉ ሁለት ደብዳቤዎች ለኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እና ለኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን አሳውቋል ያለ ሲሆን፤ እነዚህ ሁለት ተቋማት አባሎታችን የግፍ እስረኛ መሆናቸውን በመገንዘብ አስቸኳይ መፍትሄ እንዲያገኙ የበኩላቸውን ሚና እንዲጫወቱ አሳስቧል ብሏል።

14/08/2023

ኢሰመኮ የጸጥታ ኃይሎች ከህግ አግባብ ውጭ በሰላማዊ ሰዎች ላይ ግድያ መፈጸማቸውን ገለጸ

በአማራ ክልል የጸጥታ ኃይሎች ሆነብለው ከህግ አግባብ ውጭ በሰላማዊ ሰዎች ላይ ግድያ መፈጸማቸውን የሚያሳይ ተአማኒ መረጃ እንደደረሰው የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል።
ኢሰመኮ በክልሉ ባለው ወቅታዊ ሁኔታ ዙሪያ ዛሬ ባወጣው መግለጫ ባህርዳር ሰላማዊ ሰዎች ከቤታቸው ውጭ መግደላቸውን እና የተወሰኑ ወጣቶች ደግሞ ኢላማ ተደርገው መደብደባቸውን ገልጿል።
በጎንደር የተለያዩ አካባቢዎች፤ በሽዋሮቢት እና በደብረ ብርሃን ከተሞች ተመሳሳይ ድርጊት በጸጥታ ኃይሎች መፈጸሙን የሚያስረዳ ተአማኒ መረጃ ደርሶኛል ብሏል። ኢሰመኮ ዝርዘር ሁኔታው ተጨማሪ ምርመራ እንደሚያስፈልገው ገልጿል።
ተፋላሚ ሀይሎች ያለምንም ቅደመ ሁኔታ ግጭቶችን እንዲያቆሙ፣ ለሰላማዊ ንግግር ስፍራ እንዲያመቻቹና ግጭቱ በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ጥሪ አቅርቦ በክልሉ በሰብዓዊ መብቶች ላይ እያሳደረ ያለውን ተፅዕኖ እየተከታተለ መሆኑን አስታውቋል፡፡
በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በከባድ የመድፍ ተኩስ ጭምር ንጹሀን ዜጎችን ከጉዳት ባልጠበቀ መልኩ ውጊያ በመካሄድ ላይ በመሆኑ ሰላማዊ ዜጎች ህይወታቸውን እያጡ ነውም ብሏል።
ኮሚሽኑ በሪፖርቱ መንገድ ለመዝጋት የሞከሩ ሰላማዊ ተቃዋሚዎች ጭምር መገደላቸውን ፣ እስር ቤቶችና ፖሊስ ጣቢያዎች መሰበራቸውን፤ የጦርመሣሪያዎችና ጥይቶች ከመዘረፋቸው ባለፈ በቅድመ ፍርድ ያሉ እና ታራሚዎችም አመልጠዋል ብሏል፡፡ በክልሉ መንግስት ስር በተለያዩ የስልጣን እርከን ላይ ያሉ አመራሮች መገደላቸውንም ጠቅሷል።
በተለያዩ አካባቢዎች እንደ ኤሌክትሪክ ሐይል፣ ውሃ፣ ባንክ፣ ሆስፒታል፣ ትምህርት ቤቶች፣ ሰልክ፣ ኢነንተርኔት ያሉ መሠረታዊ አገልገሎቶች ተቋርጠዋል ብሏል፡፡
ከአማራ ክልል ውጪ በአዲስ አበባ በሚኖሩ የአማራ ማንነት ባላቸው ሰዎች ላይም መፈጸማቸውን አክሏል።
በመሆኑም የፌደራሉ መንግስት የጅምላ እስርን እንዲያቆም፣ ከህግ አግባብ ውጪ የታሰሩ ዜጎች እንዲፈቱ፣ የሰብዓዊ መብት ተቋማት ታሳሪዎችን እንዲጎበኙ እንዲፈቅድ ሲል አሳስቧል።

14/08/2023

በፍኖተ ሰላም በተፈጸመ ጥቃት ቢያንስ 25 ሰዎች ሲገደሉ ከ50 በላይ መቁሰላቸው ተገለጸ

በአማራ ክልል በምዕራብ ጎጃም ዞን ዋና ከተማ በሆነችው ፍኖተ ሰላም ከተማ ላይ በተፈጸመ ጥቃት ቢያንስ 25 ሰዎች ሲገደሉ፣ ከ50 በላይ የሚሆኑ ሰዎች ላይ ጉዳት መድረሱን ነዋሪዎች እና የሆስፒታል ምንጮች ተናግረዋል።

በፍኖተ ሰላም ከተማ እሁድ እለት ረፋድ ላይ ያጋጠመው ሁኔታ በድሮን የተፈጸመ መሆኑን አንድ የከተማው ነዋሪ ተናግሮ ኢላማ የተደረገውም በከተማዋ አደባባይ ላይ ቆሞ የነበረ ሲኖትራክ የተባለ የጭነት መኪና መሆኑን ገልጿል።
በቦታው በሲኖትራክ ተጭነው ሲሄዱ የነበሩ ታጣቂዎች አደባባዩ አካባቢ ቆመው ነበር። ጥቃቱ እነርሱን ኢላማ ለማድረግ ነው። ነገር ግን ያ ሲኖትራክ ቦታውን ከለቀቀ ከ20 ደቂቃ በኋላ ነው ፍንዳታው የደረሰው። ከዚያም በአይሱዙ ላይ የነበሩ ሌሎች ወጣቶች እና በአካባቢው ይንቀሳቀሱ የነበሩ ሰዎች ላይ ጥቃቱ ተፈጸመው” ብሏል።
የምዕራብ ጎጃም ዞን መቀመጫ በሆነችው ፍኖተ ሰላም ከተማ ላይ የተፈጸመውን ጥቃት ተከትሎ በርካታ ሰዎች መሞታቸውን እና ጉዳት እንደደረሰባቸው ነዋሪዎች ተናግረዋል።
ነገር ግን በጥቃቱ የሞቱ ሰዎች ቁጥር በከተማዋ ካለው ዋነኛ የመንግሥት ሆስፒል ባተገኘው መረጃ መሠረት 26 ሰዎች በጥቃቱ መገደላቸውን ተረድቷል።
በበርካታ የአማራ ክልል ውስጥ በፋኖ ታጣቂዎች እና በመንግሥት ኃይሎች መካከል የሚካሄደው ግጭት ከዋና ዋና ከተሞች በመውጣት በሌሎች አካባቢዎች እየተካሄደ መሆኑን ነዋሪዎች ተናግረዋል።
ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈቀዱ የፍኖተ ሰላም ሆስፒታል የሕክምና ባለሙያ የደረሰውን ጥቃት ተከትሎ ወደ ሆስፒታሉ በርካታ ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸው መምጣታቸውን የተናገሩ ሲሆን እስካሁን ከ70 በላይ ተጎጂዎች ወደ ሆስፒታላችን መጥተዋል ብለዋል፡፡ የሆስፒታሉ ዶክተር ጨምረውም በጥቃቱ ሕይወታቸው ካለፈው ሰዎች መካከል 22 የሚሆኑት ጥቃቱ እንደተፈጸመ እዚያው በቦታው የሞቱ ሲሆን፣ ሌሎች አራት ሰዎች ደግሞ ለሕክምና ሆስፒታል ከደረሱ በኋላ ሕይወታቸው እንዳለፈ ተናግረዋል፡፡ ዶክተሩ ጉዳት ለደረሰባቸው ሰዎች አስፈላጊ የሆኑ የግብአቶች እጥረት ስላለ አራቱን ሰዎች ለመርዳት ተቸግረው እንደነበር ገልጸዋል።
በአሁኑ ወቅትም በጥቃቱ ምክንያት ጉዳት ደርሶባቸው በሆስፒታሉ በሕክምና ላይ የሚገኙ 55 ሰዎች እንዳሉ እና ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች እየመጡ መሆናቸውን የሆስፒታሉ ምንጮች ገልጸዋል።
ትናንት እሁድ ካጋጠመው ጥቃት ጋር በተያያዘ ጉዳት ደርሶባቸው በአጠቃላይ 81 ሰዎች ወደ ፍኖተ ሰላም ሆስፒታል እና ጉዳት ደርሶባቸው ቤታቸው የቀሩ፤ ሰዎች ስላሉ እንዲሁም ሞተው ወደ ሆስፒታል ሳያመጡ የቀሩ እንዲሁም ወደ ሌላ የሕክምና ተቋም የሄዱ ሊኖሩ ስለሚችሉ፣ በጥቃቱ የሞቱ እና ጉዳት የደረሰባቸው ሰዎች አሃዝ ከዚህም በላይ ከፍ ሊል እንደሚችል ሐኪሙ ገልጸዋል።

አንድ የከተማዋ ነዋሪ ደግሞ የእኔን አራት ጓደኞቼን ጨምሮ ከ40 በላይ ሰዎች ተገድለዋል፣ ሰዉ በድንጋጤ ሁሉም በየቤቱ ስለተቀመጠ መረጃ ባለመሰብሰቡ እንጂ የጉዳቱ መጠን ከዚህም በላይ ሊሆን ይችላል ሲል የዘገበው ቢቢሲ ነው።

14/08/2023

የሸኔ ታጣቂዎች ወደ ሰሜን ሸዋ ደራ ወረዳ እየገቡ መሆናቸውን ነዋሪዎች ገለጹ

በኦሮሚያ ክልል ሰሜን ሸዋ ዞን ደራ ወረዳ የሸኔ ታጣቂዎች በወረዳው የገጠር ቀበሌዎች በስፋት እየተንቀሳቀሱ መሆናቸውን ነዋሪዎች አስታውቀዋል፡፡
የወረዳው ነዋሪዎች ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው መንግስ በሽብርተኝነት የፈረጃቸውን የቡድኑ ታጣቂዎች ወደ ወረዳው የገጠር ቀበሌዎች እየገቡ መሆናቸውን ገልጸው፤ ታጣቂዎቹ ከሰሞኑ በስፋት መንቀሳቀስ በመጀመራቸው ስጋት እየፈጠረባቸው መሆኑንም ተናግረዋል።
ታጣቂዎቹ ከዚህ ቀደም በወረዳው በተደጋጋሚ ባደረሱት ጥቃት በርካታ ዜጎች መገደላቸውንም ነዋሪዎቹ አስታውሰው በወረዳው የገጠር ቀበሌ ይኖሩ የነበሩ ዜጎች ታጣቂዎችን ሸሽት ወደ ወረዳዋ ከተማ ጉንዶ መስቀልና ወደሌሎች አካባቢዎች መሰደዳቸውን ተናግረዋል።
ሸኔ ከሁለት ዓመት በፊት ጀምሮ ወደ ወረዳው በመግባት ዜጎችን በማገት ገንዘብ መቀበል እንዲሁም ግድያና ማፈናቀል እያደረሰ መሆኑ የተነገረ ሲሆን፤ በተለይም የደራ ወረዳን ከሰላሌ ጋር የሚያገናኘውን የጀማን ድልድይ በመቆጣጠሩ የወረዳዋ ነዋሪዎች በአማራ ክልል መርሐቤቴ ወረዳ በኩል ወደ አዲስ አበባ እንዲሄዱ መገደዳቸው ተገልጿል፡፡

14/08/2023

በአዲስ አበባ፣ ሸገር፣ ቢሾፍቱ እና ወልቂጤ ከተሞች ማንነትን መሰረት ያደረገ የጅምላ እስር መኖሩ ተገለጸ

በቅርቡ በአዲስ አበባ ዙሪያ በተዋቀረው ሸገር ከተማ አስተዳደር፣ ወልቂጤ እና ቢሾፍቱ ከተሞች እንዲሁም በመዲናዋ ኮተቤ፣ ሳሪስ፣ ቄራ፣ ቦሌ ቡልቡላ፣ ሃና ማሪያም እና የተለያዩ ቦታዎች ላይ የጅምላ እስር መኖሩን ነዋሪዎች ገልጸዋል።
በአዲስ አበባ ዙሪያ በተዋቀረው ሸገር ከተማ አስተዳደር እንዲሁ ማንነትን መሰረት ያደረግ እስር በስፋት እየተፈጸመ ነው የተባለ ሲሆን፤ ሥሜ እንዳይጠቀስ ያሉ ግለሰብ በተለይ በሰበታ ከተማ በርካታ የአማራ ተወላጆች ታስረዋል ብለዋል።
ለአብነትም የሚፈልጉትን ሰው ሥም ዝርዝር የያዙ የኦሮሚያ ፖሊሶች ከብሔራዊ አልኮልና አረቄ ፋብሪካ አራት ሰዎችን እንዲሁም በቅርብ እርቀት ከሚገኘው ከባለዛፍ ፋብሪካ ስምንት የአማራ ተወላጆችን ወስደዋል ያሉ ሲሁን፤ የሰበታ ማረሚያ ቤት በእሰረኞች መጨናነቁን እስረኞችን ለመጠየቅ ከሄዱ የተመረጡ ሰዎች መረጃው እንደደረሳቸው ገልጸው፤ የሚመለከተው አካላት በንጹሃን ላይ የሚደርሰውን በደል ሊያስቆም ይገባል ብለዋል።
ሥሜ እንዳይጠቀስ ያሉ ሌላኛው በጉራጌ ዞን የወልቂጤ ከተማ ነዋሪ ለአዲስ ማለዳ እንደተናገሩት፤ ሰሞኑን በወልቂጤ ከተማ ባልተለመደ መልኩ የክልሉ ፖሊስ እና የፌዴራል ፖሊስ አባላት በጋራ በመሆን በተለይም የአማራ ብሔር ተወላጆች በብዛት በሚኖሩባቸው ስፍራዎች ቅኝት ያደርጉ እንደነበር ገልጸዋል፡፡
የጸጥታ ኃይሎቹ ሌሊት ላይ ወደ መኖሪያ ቤታቸው በማቅናት እና በር በማስከፈት እንዲሁም በኃይል ገንጥሎ በመግባት፤ ያላንዳች ምክንያት እና የፍርድ ቤት ትዕዛዝ በመያዝ ወደ እስር ቤቶች እና ወዳልታወቀ ስፍራ እንደሚወሰዷቸውም አስረድተዋል፡፡ የጸጥታ ኃይሎች ሰዎችን በሚይዟቸው ወቅትም አካላዊ ድብደባ እና የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንደሚፈጽሙባቸው ተናግረዋል፡፡
ነዋሪዎቹ ድርጊቱ በአማራ ክልል በአገር መከላከያ ሠራዊት እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ካለው ውጊያ ጋር በተያያዘ ሊሆን እንደሚችል ጠቅሰው፤ ምንም ዓይነት ወንጀል ላይ ያልተሳተፉ ንጹሃንን በጅምላ ማሰር ተገቢ አካሄድ አይደለም ሲሉ ገልጸዋል።
ዜጎች ያቀረቡትን ቅሬታ መሰረት በማድረግ የመንግሥት አካላት የተጠየቁ ሲሆን፤ የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ኮማንደር ማርቆስ ታደሠ በአካል መጥታቹ ያለውን ሁኔታ መታዘብ ትችላላችሁ ከማለት ውጭ በስልክ መረጃ ከመስጠት መቆጠባቸው ተገልጻል፡፡

14/08/2023

የከምባታ ዞን ምክር ቤት የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የአስፈጻሚ ቢሮ አደረጃጀትን ሳይቀበል ቀረ

የከምባታ ጠምባሮ ዞን ምክር ቤት በአዲስ መልክ ለሚዋቀረው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የተዘጋጀውን የአስፈጻሚ ቢሮዎችና ተቋማት አደረጃጀት ሳይቀበለው መቅረቱ ተገልጿል፡፡
ምክር ቤቱ አደረጃጀቱን ያልተቀበለው በዞኑ ዋና ከተማ ዱራሜ በተጠራው አስቸኳይ ጉባዔ ላይ ከአባላቱ ጋር ከተወያየ በኋላ ባሳለፈው የውሳኔ ሀሳብ መሠረት ነው ተብሏል፡፡
በሚመሠረተው ክልል ከሚገኙት ሠላሳ ሁለት ተቋማት መካከል ለከምባታ ጠምባሮ ዞን አንድ የግብርና ቢሮ ብቻ መሰጠቱ ያስቆጣቸው የምክር ቤቱ አባላት፤ አደረጃጀቱ አድሏዊ፣ ኢፍትሃዊ እና የዞኑን በእኩል የመልማት መብት የነፈገ ነው ሲሉ ተችተዋል፡፡
ወደ ክልል ምሥረታ ከመገባቱ በፊት አደረጃጀቱ እንደገና እንዲሻሻል ጥያቄው በምክር ቤቱ ዋና አፈ ጉባዔ አማካኝነት ለፌዴሬሽን ምክር ቤት እንዲቀርብ ጉባዔው በሙሉ ድምፅ ማሳለፉን የምክር ቤቱ አባላት ወይዘሮ ውብዓለም በቀለ እና አቶ መሀመድ ኤደሞ ለዶቼ ቬለ ተናግረዋል፡፡
የደቡብ ክልል መንግሥት ግን የዞን ምክር ቤቱ ውሳኔ ላይ እስከአሁን የሰጠው ምላሽ አለመኖሩ ተዘግቧል ፡፡

14/08/2023

የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል በአማራ ክልል ሰብዓዊ ድጋፍ ለማድረግ መቸገሩን አስታወቀ

ከሰሞኑ በአማራ ክልል በተከሰተው ግጭት የደረሰውን ጉዳት መጠን በትክክል ለማወቅ አልቻልኩም ያለው የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር፣ ለደረሰው ጉዳት ተገቢውን ሰብዓዊ ድጋፍ ለማድረግ መቸገሩን አስታውቋል፡፡
የተከሰተው ግጭት ድንገተኛ ከመሆኑም በላይ መንገዶች በመዘጋታቸው የማኅበሩ ቅርንጫፍ ሠራተኞች ተንቀሳቅሰው ሰብዓዊ ድጋፍ ማድረግ አለመቻላቸውን የቀይ መስቀል ማህበር የቦርድ አባል ኢንጅነር ጌታሁን ሁሴን ገልጸዋል፡፡
ኢንጅነር ጌታሁን አክለውም ‹‹ሁሉንም ወገኖች የምንለምነው ተንቀሳቅሰን ድጋፍ ለማድረግና ሰብዓዊ ድጋፋችንን ለመስጠት እንድንችል ተባብሩን ነው፤›› ሲሉ ጠይቀዋል፡፡
በግጭቱ ምክንያት ዜጎች ከዚህ የከፋ ጉዳት እንዳይደርስባቸው ማኅበሩ አስፈላጊውን ሰብዓዊ ድጋፍ እንዲያደርግ ሁሉም አካላት ተገቢውን ድጋፍ እንዲያደርጉ የኢትዮጵያ ቀይ መስቀል ማኅበር ዋና ጸሐፊ አቶ ጌታቸው ታዓ ጠይቀዋል፡፡
የቀይ መስቀል ማኅበር ሠራተኞች፣ አምቡላንሶችና በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች የቀይ መስቀልን ዓርማ ይዘው በሚንቀሳቀሱበት ወቅት ሁሉም አካላት አስፈላጊውን ትብብር እንዲያደርጉ ማኅበሩ አበክሮ ጠይቋል፡፡
በተያያዘም በአማራ ክልል ባለው የፀጥታ ችግር ምክንያት የመንገድ መዘጋት፣ የሕክምና ግብዓት ችግር፣ የኦክስጂንና የደም እጥረት እየተከሰተ መሆኑን የአማራ ክልል ሕክምና ማኅበር ነሐሴ 3 ቀን 2015 ዓ.ም በይፋዊ የማኅበራዊ ትስስር ገጹ ይፋ አድርጎ ነበር፡፡

10/08/2023

በትግራይ መጠለያዎች የሚገኙ ኤርትራውያን ስደተኞች ችግር ውስጥ መሆናቸውን ገለጹ

ላለፉት ዐሥር ወራት የእርዳታ እህል እንዳልተሰጣቸው የገለጹት፣ በትግራይ መጠለያ ጣቢያዎች የሚገኙ ኤርትራውያን ስደተኞች፣ በእጅጉ መቸገራቸውን ተናግረዋል፡፡
ለደኅንነታቸው በመስጋት ማንነታቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ አስተያየት ሰጭዎች፣ እንደሚሉት፣ በማይ ዓይኒ እና በዓዲ ሓሩሽ የመጠለያ ጣቢያዎች ውስጥ፣ 1ሺሕ700 ስደተኞች እንደሚኖሩ ገልፀው በመጠለያ ጣቢያዎቹ፣ መሠረታዊ አገልግሎት ባለመኖሩ፣ ለከባድ ችግር እንደተጋለጡ አስታውቀዋል፡፡ በሕክምና ዕጦት ምክንያት፣ በቅርቡ የ20 ሰዎች ሕይወት ማለፉንም ገልጸዋል፡፡
በሁሉም አቅጣጫዎች መሳሪያ በደቀነበት አካባቢ እና ስጋት ውስጥ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ነው የምንኖረው ያሉት ስደተኞቹ የአካለዊ እና ስነ ልቦናዊ ጉዳት እንደደረሰባቸው ተናግረዋል፡፡
ህይወታችን አልባት አጥቷል አቤቱታችን የሚሰማ አካል አልተገኘም ያሉ ሲሆን ከየትኛውም አካል የዲፕሎማሲያዊ፣የገንዘብ አንዲሁም የቁሳቁስ ድጋፍ አንዲደረገልን ሰንል በፈጣሪ ሰም አንጠይቃለን ብለዋል፡፡
የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር/UNHCR/ እንደሚለው“ስደተኞቹ፣ በዚያ አካባቢ ሆነው አገልግሎት ማግኘት እንደማይችሉ አስቀድመን ነግረናቸዋል፤ አሁንም ወደ ቦታው መግባት አንችልም፤” ማለታቸውን የዘገበው ቪኦኤ ነው፡፡

10/08/2023

በትግራይ የምግብ እርዳታ ከተቋረጠ ወዲህ 1411 ሰዎች በረሃብ መሞታቸው ተገለፀ

በትግራይ የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት ከተቋረጠ ወዲህ ባለው ጊዜ ብቻ በትግራይ 1411 ሰዎች በረሃብ ምክንያት ሞተዋል ሲል የክልሉ አስተዳደር አስታወቋል።
የክልሉ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮምሽን ኮምሽነር ዶክተር ገብረሕይወት ገብረእግዚአብሔር እንደገለፁት እነዚህ በረሀብ ምክንያት ሕይወታቸው ያለፈ 1411 ሰዎች ሽማግሌዎች፣ ሴቶች፣ ህፃናት ናቸው ብለዋል፡፡
የምግብ እርዳታው ከቆመ በኃላ ከዞኖች፣ ወረዳዎች ደረሰን ባሉት ሪፖርት የሟቾቹ ቁጥር ምዕራብ ትግራይ ዞን፣ የደቡብ ትግራይ ዞን 6 ወረዳዎች፣ የማእከላዊ ዞን 22 ወረዳዎች እንዲሁም የመቐለ 7 ክፍለ ከተሞች እንደማይጨምር ዶክተር ገብረሕይወት ተናግረዋል። በክልሉ የነበረው ጦርነት ከቆመ ወራት ቢያልፉም፥ ጦርነቱ የፈጠረው ማሕበራዊ ቀውስ ግን አሁንም በጉልህ እንደሚታይና ከ6 ሚልዮን በላይ የሚሆን ህዝብ የምግብ እርዳታ ፈላጊ መሆኑ ነው የተገለፀው ።
ሕይወት አድን ድጋፍ ያደርጉ የነበሩ ዓለምአቀፍ ለጋሾች የእርዳታ እህሉ ላልተፈለገ ዓላማ ውልሏል በሚል ምክንያት ካለፈው የካቲት ወር ጀምሮ ያቋረጡትን ልገሳ ማቅረብ መጀመሩ የተዘገበ ቢሆንም
የክልሉ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮምሽን እንደገለፁት የተጀመረው፥ ለረዥም ግዜ በትግራይ ተቋርጦ የነበረ የሴፍትኔት ፕሮግራም እንጂ የአስቸኳይ ሕይወት አድን ሰብአዊ እርዳታ አለመሆኑ አስገንዝበዋል። ኮምሽነሩ ዶክተር ገብረሕይወት፥ ዓለምአቀፍ ለጋሾች እስካሁን በትግራይ ላሉ እርዳታ ፈላጊዎች ያቀረቡት እገዛ የለም ብለዋል።ጉዳዩ ላይም በዓለም የምግብ ድርጅት (WFP) ምንም አይነት ምላሽ አለመስጠቱን የዘገበው ዶቼቨለ ነው፡፡

10/08/2023

የሕፃናት አድን ድርጅት ግጭት በከፋባቸው የዐማራ ክልል አካባቢዎች ርዳታ እንዲቀርብ ተጠየቀ

የግጭት መባባስን ተከትሎ፣ የአስቸኳይ ጊዜ ዐዋጅ በታወጀበት የዐማራ ክልል፣ የሰብአዊ ርዳታ ተደራሽነት እንዲቀጥል ይደረግ ዘንድ፣ ሕፃናት አድን ድርጅት፣ ተማፅኖ አቀረቧል።
በኢትዮጵያ የሕፃናት አድን ድርጅት ሥራ አስኪያጅ ዜቪዬር ዡቤር፣ በክልሉ በአሳሳቢ ሁኔታ የተባባሰው ግጭት፣ ሕፃናትን ጨምሮ ቤተሰቦችን ለአደጋ እያጋለጠ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የቅርብ ጊዜው[የሰሜን ኢትዮጵያ] ጦርነት ቁስል ሳይደርቅ፣ የሕፃናት ሕይወት ለአደጋ እየተጋለጠ ነውያሉ ሲሆን እኛ፣ እንደ ሰብአዊ እርዳታ ድርጅት፥ ተዋጊ ወገኖች፣ ለሲቪሎች ደኅንነት ቅድሚያ እንዲሰጡ ጥሪ እናቀርባለን ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በቀደመው ግጭት የተፈናቀሉትን 580 ሺሕ ሰዎች ጨምሮ፣ ችግር ላይ ላሉት በሙሉ፣ ሰብአዊ ረድኤት ማቅረብ እንዲቻል እንማፀናለንም” ብለዋል፡፡
ሕፃናትን፥ ከሁከት፣ ከመፈናቀል፣ ከረኀብ፣ ከስቆቃ መጠበቅ ይኖርብናል፤ ያሉት የድርጅቱ ሥራ አስኪያጅ፣ ለአደጋ የተጋለጡ ቤተሰቦች፣ ጥበቃ ሊያገኙና መሠረታዊ ሰብአዊ ርዳታ ሊቀርብላቸው እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

10/08/2023

13 አገር አቋራጭ የጭነት ትራንስፖርት ባለንብረቶች በግብር አከፋፈል ላይ ቅሬታ እንዳላቸዉ ገለጹ

በአገር አቋራጭ ትራንስፖርት አገልግሎት ላይ በተደረገ የግብር አከፋፈል አሠራር ለውጥ ሥራችንን ለመሥራት ተቸገርን ያሉ 13 አገር አቋራጭ የጭነት ትራንስፖርት ባለንብረቶች አክሲዮን ማኅበራት፣ ቅሬታቸውን አቅርበዋል፡፡
የጭነት ትራንስፖርት ተሽከርካሪ ባለንብረቶቹ ዓመታዊ ግብራቸውን ከዚህ በፊት በነበሩት ዓመታት በቁርጥ ግብር ሲከፍሉ የነበረ ሲሆን፣ በለውጡ መሠረት የቁርጥ ግብሩ ቀርቶ ተሽከርካሪዎቹ ባስገቡት ገቢ እንዲሆን ተደርጓል።
አሠራሩ ተግባራዊ ሲደረግ የነበረው በሥራ ባህሪው የተነሳ የአገር አቋራጭ ትራንስፖርት አገልግሎት በሚሰጥበት ጊዜ ሕጋዊ ደረሰኝ መመዝገብና የሒሳብ መዝገብ ለማያያዝ አስቸጋሪ በመሆኑ እንደነበር፣ ማኅበራቱ ለትራንስፖርት አሠሪዎች ፌዴሬሽን በጻፉት ደብዳቤ ቅሬታቸውን ለመንግሥት አቀርበዋል፡፡

10/08/2023

የአስቸኳይ ጊዜ ጠቅላይ መምሪያ ዕዝ በአማራ ክልል የሚተገበሩ ትዕዛዝና ክልከላዎችን አስተላለፈ

የአስቸኳይ ጊዜ ጠቅላይ መምሪያ ዕዝ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ በአማራ ክልል ያከናወናቸውን የመጀመሪያ ምዕራፍ ተግባራት መገምገሙን የገለጸ ሲሆን፤ በቀጣይ በክልሉ የሚተገበሩ ትዕዛዝና ክልከላዎችን አስተላልፏል።
በግምገማውም የዕዙ የመጀመሪያ ምዕራፍ ዕቅድ በባሕር ዳር፣ ደብረ ማርቆስ፣ ደብረ ብርሃን፣ ላሊበላ፣ በጎንደርና በሸዋ ሮቢት አካባቢ ከተሞቹን ወደ ሰላማዊ ሁኔታ መመለስ እንደነበርና ። እነዚህ አካባቢዎች የተመረጡት ብዙ ሕዝብ የሚኖርባቸው፣ ከፍተኛ የንግድና የቱሪስት እንቅስቃሴ ያለባቸው፣ የፖለቲካና የኢንዱስትሪ ማዕከላት በመሆናቸው መሆኑን ጠቅሶ በአሁኑ ሰዓት ከተሞቹ ከስጋት ነጻ ሆነዋል ብሏል። በቀጣይም ከተሞቹ በአጭር ጊዜ ወደ ተሟላ ሰላማዊ እንቅስቃሴ እንዲመለሱ የሚያደርግ መሆኑን አስታውቋል፡፡
በመጀመሪያው ምዕራፍ የተያዘው ዕቅድ እየተጠናቀቀ በመሆኑ የሕዝብን ሠላምና ደህንነት ለማስጠበቅ የወጣ የሚኒስትሮች ምክር ቤት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ቁጥር 6 /2015 አንቀጽ 5 መሰረት የአስቸኳይ ጊዜ ጠቅላይ መምሪያ ዕዙ ትዕዛዞችና ክልከላዎች ደንግጓል።
በዚህም ከዛሬ ሐሙስ ነሐሴ 4 ጀምሮ በተጠቀሱት ከተሞች መደበኛ የአውሮፕላን በረራ ይጀመራል ብሏል፡፡ ከባጃጅና ከሞተር ሳይክል በስተቀር ሁሉም ዓይነት የከተማ የትራንስፖርት አገልግሎቶች ወደ አገልግሎት እንዲገቡና የመንግሥት፣ የማኅበረሰብ አገልግሎት፣ የንግድ፣ የጤና፣ የፋይናንስ፣ የመሳሰሉት ተቋማት አገልግሎት እንዲሰጡ እንደሚደረግም አስታውቋል።
የአስቸኳይ ጊዜ ጠቅላይ መምሪያ ዕዙ ፈቃድ ውጪ በክልሉ ከተሞች የአደባባይ ስብሰባ፣ ሰልፍ እና መሰል እንቅስቃሴዎችን ማድረግ ፈጽሞ የተከለከለ እንደሆነ እና ለጸጥታ ሥራ ከሚንቀሳቀሱ የህግ አስከባሪ አካላት እና ከነዚህ አካላት ፈቃድ ውጭ የጦር መሣሪያ ይዞ መዘዋወር እንደማይቻል ነው የገለፀው።
ወቅታዊ ሁኔታን ሰበብ በማድረግም ግለሰቦችን ከመደበኛው ህግ አግባብ ውጪ ማሰር እና ማቆየት፣ የንግድ ቤቶችን ማሸግ እና መሰል እርምጃዎችን መውሰድ አይቻልም ያለ ሲሆን የተገለፁትን ትዕዛዞችና ክልከላዎችን በሚጥሱ ላይ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አንቀጽ 7 መሰረት ሃይልን በመጠቀም፣ እንዲሁም ሌሎች አግባብነት ያላቸውን እርምጃዎችን በመውሰድ ትዕዛዝና ክልከላዎችን እንዲያስፈጽሙ ለሁሉም የህግ አስከባሪ አካላት ጥብቅ መመሪያ ተሰጥቷል ብሏል።

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በቀጣይ ሶስት ቀናት ወደ ደሴ (ኮምቦልቻ)፣ ጎንደር፣ ላሊበላ እና ባህርዳር የሚደረጉ በረራዎችን ሰርዟልየኢትዮጵያ አየር መንገድ በመጪው ረቡዕ፣ ሐሙስ እና ዓርብ ወደ...
08/08/2023

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በቀጣይ ሶስት ቀናት ወደ ደሴ (ኮምቦልቻ)፣ ጎንደር፣ ላሊበላ እና ባህርዳር የሚደረጉ በረራዎችን ሰርዟል

የኢትዮጵያ አየር መንገድ በመጪው ረቡዕ፣ ሐሙስ እና ዓርብ ወደ ደሴ (ኮምቦልቻ)፣ ጎንደር፣ ላሊበላ እና ባህርዳር የሚደረጉ በረራዎች የተሰረዙ መሆናቸውን አስታውቋል፡፡
ወደሥፍራው ለመጓዝ ትኬት የቆረጡ ደንበኞችም ትኬታቸው ለአንድ ዓመት ያህል የሚያገለግል መሆኑን በማወቅ ወደፊት በፈለጉበት ቀን ያለምንም ተጨማሪ ክፍያ መቀየር የሚችሉ መሆኑን ገልጿል፡፡
ነገር ግን ገንዘብ ተመላሽ እንዲሆንላቸው የሚፈልጉ ደንበኞች አቅራቢያቸው ወዳሉ የአየር መንገዱ የትኬት መሻጫ ቢሮዎች ወይንም የጉዞ ወኪሎቻቸው በመቅረብ መስተናገድ ይችላሉም ብሏል፡፡

08/08/2023

በመላው ሀገሪቱ የሚታዩ ግጭቶች ያላንዳች ቅደመ ሁኔታ ቆመው በአስቸኳይ በምክክር እንዲፈቱ ጥሪ ቀረበ

የኢትዮጵያ ሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን በመላው ሀገሪቱ የሚታዩ ግጭቶች “ያላንዳች ቅደመ ሁኔታ ቆመው በአስቸኳይ በምክክር እንዲፈቱ ጥሪ አቀርቧል።
ኮሚሽኑ ባለድርሻ አካላትን በማቀራረብ፣ የልዩነት አጀንዳዎችን ሰብስቦ ለማወያየት እና ለማመካከር አመቺ ሁኔታዎችን ለመፍጠር ዝግጁ መሆኑን አስታውቋል።
ለሀገራዊ ምክክሩ የተሳታፊዎች ልየታ እየተከናወነ ባለበት ሁኔታ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች አየታዩ ያሉ “ደም አፋሳሽ ግጭቶች” የኮሚሽኑን ስራ “አዳጋች እያደረጉበት ይገኛሉ በማለት የኮሚሽኑ ዋና ኮሚሽነር ፕ/ር መስፍን አርዓያ መግለጻቸውን ኢትዮጵያ ኢንሳይደር ዘግቧል፡፡
በሌላ በኩል በአማራ ክልል የተከሰተውን ግጭት ለመፍታት በተደነገገው አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈጻጸም ወቅት የጸጥታ አካላት ያልተመጣጠነ ኃይል እንዳይጠቀሙ፣ ብሔርን መሠረት ያደረጉ ማግለሎች እና ጥቃቶች እንዳይስፋፉ እንዲሁም የጅምላ እስሮች እንዳይፈጸሙ ዘጠኝ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች በትናንት እለት ጥሪያቸውን አቅርበዋል።
ይህንን ጥሪ ካቀረቡት የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች መካከል የመብቶች እና ዴሞክራሲ ዕድገት ማዕከል (ካርድ)፣ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ተሟጋቾች ማዕከል፣ የኢትዮጵያ የሕግ ባለሙያ ሴቶች ማህበር እና የኢትዮጵያ ሴቶች ማህበራት ቅንጅት ይገኙበታል።

08/08/2023

የኢትዮጵያ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን የጳጳሳት ጉባኤ ፤ በሀገሪቱ እየተካሄደ ያለው ጦርነት ባስቸኳይ እንዲቆምና ችግሮች በውይይት እንዲፈቱ ጠየቀ

ዳግም ሞት እና ውድመት ውስጥ መግባቱ ይቅርብን በማለት ጥሪዉን ያቀረበዉ የኢትዮጵያ ካቶሊክ ቤተክርስትን የጳጳሳት ጉባኤ ባወጣዉ መግለጫ ጦርነት ለየትኛውም አይነት የፖለቲካዊ ችግር መፍትሔ ሆኖ አያውቅም ብሏል።
ፖለቲካዊ ችግር መፈታት ያለበት መከባበር ባለበት የጋራ ጥቅም በሚያስቀድም ሁኔታ በሚደረግ የፖለቲካ ውይይት ነው ያለው ጉባኤው ውይይቱ ብሶት የወለዳቸውን ምሁራንን፣ የሀገር ሽማግሌዎችን፣ የሃይማኖት አባቶችን፣ ወጣቶችን እና ሴቶችን ጭምር ያካተተ ቢሆን የበለጠ ውጤታማ እንደሚሆን ሙሉ እምነታችን ነው " ሲል ገልጿል።
ይህ እንዲሆን የመንግሥት፤የፖለቲካ ፈቃደኝነት በጣም አስፈላጊ እንደሚሆን አመልክቷል።
የኢትዮጵያ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን የጳጳሳት ጉባኤ በዚሁ መግለጫው ፤ በሀገራችን እየተካሄደ ያለው ጦርነት ባስቸኳይ እንዲቆምና በውይይት ችግሮች እንዲፈቱ መንግስትንና ተፋላሚ ወገኖችን አጥብቆ ተማጽኗል።
በዚህ በፍልሰታ ጾም ጸሎት ወቅት ልቦናችንን ወደ እግዚአብሔር እንድንመልስ ያለ ሲሆን ስለ ሰላም ፣ ፍትህ፣ ውይይት የሚጸልይ መሆኑንና ለምዕመናኖች በጎ ፊቃድ ላላቸው ወገኖች ሁሉ የሰላም ጥሪዉን አቅርቧል፡፡

Address

Addis Ababa
1000

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Harambee radio 98.7 posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Business

Send a message to Harambee radio 98.7:

Videos

Share

Category