10/05/2024
ወንጌል ለስጋም የተረፈበት ወላይታ‼️
ባዕድ አምልኮ ይመለክ ነበር። ኪቶሳ ሀውዙላ ሙሉጉሻ ወዘተ እየተባለ ሰይጣን በሚመለክበት ወላይታ ነው ከወደ አሜሪካ የምስራቹን ወንጌል ይዘው ዶክተር ቶማስ ላምቤ ብቅ ያሉት።
ዶክተሩ በቀኝ እጃቸው የነፍስ ህመም የሚያክመውን ሰማያዊውን ወንጌል ገላጭ መፅሐፍ ቅዱስ፣ በግራ እጃቸው ደግሞ የስጋን ህመም የሚያክመውን መርፌ ይዘው ተገኙ። ለመጀመሪያም ግዜ በ1921 ዓም በዎላይታ የህክምና ተቋም ገነቡ።
ወንጌልን በባዕድ አምልኮ ውስጥ ለነበረው ህዝብ አበሰሩ። እንደ አባባ ዋንዳሮ ያሉ ጥቂት አባቶች ተቀበሉ አቀጣጠሉ። የወንጌል ሰደድ እሳት ወላይታን አገኘ። ከወንጌሉ በተጨማሪ የወላይታ ህዝብ የተሻለ ትምህርትና ህክምና እንዲያገኝ የሰሩት ቶማስ ላምቤ ወላይትኛ ቋንቋን መናገራቸው ከተወላጁ ጋር ለመግባባት በር ከፍቶላቸዋል።
አዎ ዛሬ ለብዙዎች ህክምናና የጤና ትምህርት የሚሰጠው የያኔው ኦተና ሆስፒታል የዛሬው የወላይታ ሶዶ ዩኒቨርሲቲ መማሪያና ኮምፕሬሄንሲቭ ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል ተመሰረተ።
በዚህም አላበቃም ወላይታና የምስራቹ ወንጌል ያላቸው ዘርፈ ብዙ ትስስር። የወንጌል ተልዕኮ ይዞ ዛሬ በተለይ በአጥንት ህክምና በምስራቅ አፍሪካ ተመራጭ የሆነው ክርስቲያን ሆስፒታልም ወንጌል በወላይታ ከነፍስ ባሻገር ለስጋም የተረፈ በረከት ይዞ ይመጣ ዘንድ በር ከፈተ።
አዎ ዘር ጎሳ ሃይማኖት ሳይለይ ለሰው ልጅ ሁሉ ህክምና የሚሰጥ ትልቅ የጤና ቤት በዎላይታ ይገኝ ዘንድ የምስራቹ ወንጌል በረከት ሆኗል። ወንጌል ለነፍስ ብቻ ሳይሆን ለስጋም የሚተርፍ የምስራች ነው።
ጥላሁን ሁሴን