22/09/2021
የባሕርዳር ከተማ አስተዳደር ፀጥታ ምክር ቤት አስቸኳይ ውሳኔዎችን አሳልፏል።
የምክር ቤቱ ሙሉ የውሳኔ ሀሳብ ቀጥሎ ቀርቧል።
መስከረም 12/2014 ዓ.ም
የባሕርዳር ከተማ አስተዳደር ፀጥታ ምክር ቤት በከተማችን ወቅታዊ የሰላምና ፀጥታ ጉዳዮች ላይ ውይይት ካደረገ በኋላ ቀደም ሲል የትህነግ ወራሪ ኀይል በክልላችን ሰርጎ በመግባት በየከተሞች የሚያደርሰውን ጉዳት ለመቆጣጠር ተብሎ ተጥሎ የነበረውን የሰዓት እላፊን እና ሌሎች የተለያዩ ውሳኔዎችን በከተማችን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ችግሮች እንዳይስፋፉ ማስተካከያ መደረጉ ይታወሳል።
ነገር ግን በክልላችንን የተጋረጠብንን "የህልውና ጉዳይ" የአልተገነዘቡ አካላት ለከተማችን የማይመጥን አንዳንድ ህገ ወጥ እንቅስቃሴዎች እየተስተዋሉ መሆናቸውን የፀጥታ ምክር ቤቱ ገምግሟል።
ስለሆነም የሚከተሉትን መስተካከል የአለባቸው ነገሮች የፀጥታ ምክር ቤቱ ተወያይቶ ክልከላ እንዲደረግ ወስኗል።
1ኛ/ስምሪት ከተሰጠው የፀጥታ ኀይል ውጭ በከተማችን ማንኛውንም አይነት የጦር መሳሪያ ይዞ መንቀሳቀስ አስፈላጊ ሆኖ ስላላገኘው እንዲከለል ምክር ቤቱ ወስኗል።
2ኛ/ለንግድ ስራ ከተፈቀደላቸው ቦታ ውጭ የእግረኛና የተሽከርካሪ መንገድ ዘግቶ መጠጥ ቤት ማስተናገድ፣ ኮበልስቶን መንገዶችን ዘግቶ ማንኛውንም ግብይት መፈፀም በጥብቅ የተከለከለ ነው።
3ኛ/ በከተማችን በተናጥልም ሆነ በቡድን የተደራጀ የትኛውንም ህጋዊም ይሁን ህጋዊ ያልሆነ ቁማር ቤት ከፍቶ መጫዎት እና ማጫዎት ፈፅም የተከለከለ ነው።
4ኛ/ በከተማችን በመንግስት ከተፈቀደለት ተቋም ውጭ ምንም አይነት ወታደራዊ ስልጠና መሰልጠንና ማሰልጠን ፈፅሞ የተከለከለ ነው።
5ኛ/ በመጠጥ ቤቶች አካባቢ ነዋሪዎችን የሚረብሽ ሁከትና ግርግር በመፍጠር ለሰላማዊ ነዋሪዎች ስጋት መሆን እና ተዛማጅ እንቅስቃሴዎችን ማድረግ የማይፈቀድ መሆኑ በመግለፅ ተላልፎ የሚገኝ አካል ላይ ህጋዊ እርምጃ መወሰድ እንደሚችል ፀጥታ ምክር ቤቱ ወስኗል።
"የከተማችን ሰላም በጋራ እናስከብር!"
የባሕርዳር ከተማ አስተዳደር ጸጥታ ምክር ቤት
መስከረም 12/2014 ዓ.ም
ባሕርዳር