In Christ

In Christ Blessed is the man who gets the opportunity to devote his life to something bigger than himself.

ትንሽ ስለ ሰሙነ ሕማማትእሮብ፣ አርብ እና እሁድበሕማማት ሳምንት ሰባቱም ቀን የየራሳቸው ታሪክ ቢኖራቸውም እንዚህ ሶስት ቀኖች ግን  በክርስቶስ ሞት ላይ ቀጥተኛ አስተዋጽዎ በማድረግ ከሳምንቱ...
05/02/2024

ትንሽ ስለ ሰሙነ ሕማማት
እሮብ፣ አርብ እና እሁድ

በሕማማት ሳምንት ሰባቱም ቀን የየራሳቸው ታሪክ ቢኖራቸውም እንዚህ ሶስት ቀኖች ግን በክርስቶስ ሞት ላይ ቀጥተኛ አስተዋጽዎ በማድረግ ከሳምንቱ ቀደምት ናቸው።

በሐዋ ማቴዎስ እና ማርቆስ የታሪክ አመዘጋገብ መሠረት በዕለተ እሮብ ሦስት ነገሮች ተፈጽመዋል።

1. የካህናት አለቆች፣ የሕዝብ ሽማግሌዎችና ጸሐፍት ፈሪሳውያን በጌታችን ላይ ተማክረዋል።
2. ጌታችን በስምኦን ቤት ሳለ አንዲት የተጸጸተች ሴት ሽቱ ቀብተዋለች።
3. ከዳተኛው ይሁዳ ጌታችንን አሳልፎ ለመስጠት ከጸሐፍት ፈሪሳውያን እና አለቆች ዘንድ ሠላሳ ብር ለመቀበል ተስማምቷል።

እሮብ እና ይሁዳ (ምህረት የጀመረበት ቀን)

ስለ አስቅሮቱ ይሁዳ መጻፍ የሚማርክ ነገር እንዳልሆነ የምናውቀው አራቱ ወንጌላት አስገዳጅ ካልሆነባቸው በስተቀር ስለ ይሁዳ ብዙ ነገር ባለመጻፋቸው ነው። ክህደት እና አስመሳይነት ምን ደስ ይልና።
ክህደቱ ከጌታው ጋር እየተመላለሰ በውጪ ሊሸጠው ማሰቡ አስመሳይነቱ ደግሞ ‹አሳልፌ የምሰጥህ እኔ እሆንን? ብሎ በድፍረት አይን አይኑን እያየ መጠየቁ ነው። ማቴ 26፤25 . . .

መቼም ጌታ በዕለተ አርብ በጠላቶቹ እጅ ከተሠቃየው ሥቃይ ይልቅ በወዳጁ ይሁዳ ምክንያት በዕለተ እሮብ የተሠቃየው የኅሊና ሥቃይ ይከፋል ብዬ አስባለሁ። ሳምንቱ የመስቀሉን ሞት የታገሰበት ብቻ ሳይሆን የሽንገላ መሳምን ያሳለፈበት ሳምንት ነበር።እንደ ዳታን እና አቤሮን መሬት ተሰንጥቃ ስላልዋጠችው፣ ምላሱ ከጉሮሮው ጋር ስላልተጣበቀ፣ ሽንገላ ያወሩት እንደበቱ ዲዳ ባለመሆናቸው የምህረት ጥጉን ከጲላጦስ በፊት በዚህ ሰው አየንበት።

እለተ እሮብ ታላቁ የአይሁድ ሸንጎ(the great sehedrin) ሰባ ሁለት አባላቱን ይዞ በሊቀ ካህኑ ቀያፋ አስተናባሪነት ተሰይሟል። ይህ መሰየም እርስ በእርሳቸው በነገረ ሃይምኖትም ሆነ በሃገራዊ ሁኔታ ብዙውን ተስማምተው የማያቁትን የአይሁድ ገዢዎች በጌታ መገደል ላይ ሊያስማማ ነው። ዳዊት ‹አለቆችም በእግዚአብሔርና በመሲሁ ላይ በአንድነት ተሰባሰቡ› መዝ 2:2 እንዳለ።

ይሁዳም የተሰበሰቡበትን አላማ ሊያስፈፅም ዳር ቆሟል: ለድርድር እንኳን ሳይግደረደር ‹ምን ልትሰጡኝ ትወዳላችሁ› ብሎ ተመኑን ለእነርሱ አሳልፎ ሰጣቸው። ይህም የገንዘብ ጥልቅ ፍቅሩን ያሳየናል።

ምናልባትም በውጪ ባሉት በጥፊ ከመመታት ይልቅ ያለተመን መሸጥ ምን ያህል ልብ እንደሚሰብር ማሰብ ቀላል ነው። መቼም የተሰበሰቡት አይሁድ እንደመሆናቸው ህግ ስለሚያውቁ ቢያንስ «በሬው ወንድ ባሪያ ወይም ሴት ባሪያ ቢወጋ፡ የበሬው ባለቤት ሠላሳ ስቅል ለጌታቸው ይስጥ» ዘጸ 21:32 የሚለውን ህግ ስለሚያውቁ ቢያንስ ከአንድ ባሪያ ዋጋ አላሳነሱትም እንጂ ሻጩማ በፈለጋችሁት ውሰዱት ብሎ ነበር።

ዳሩ ግን በዛው በእለተ እሮብ ጠዋት ከማትታወቅ እርቃ ከነበረች ሴት የሦስት መቶ ስቅል(ዲናር) ሽቶ በስምኦን ቤት እግሩ ስር ፈሶለት ነበር። እርሱ አይደለም በዛው ቀን የፈሰሰለት ሽቱ ከተሸጠበት አስር እጅ ይልቅ ነበር።

እዚጋ የተካደው ኢየሱስ በመሆኑ እንጂ ነቢዩ ኤልሳዕ ሎሌው ግያዝ የማይገባውን ገንዘብ ከሶሪያዊው ንዕማን ተቀብሎ ከሸሸገ በኋላ የንዕማን ለምጽ በአንተ ላይ ይጣበቃል ብሎ ለምጻም እንደሆነ (2ኛ ነገ 5:20-27) ወይም ሐዋሪያው ጴጥሮስ ሐናንያ እና ሰጲራ የተባሉ ባልና ሚስት ከቤታቸው ሸሽገው መንፈስ ቅዱስን ሊያታልሉና በማስመሰል በፊቱ ሊቆሙ ሲሞክሩ እንደሚቀሰፉ ሲነግራቸው (ሐዋ 5፡ 1-10) ይሁዳ ግን እስከማስመሰሉ ከነቢያትም ከሐዋሪያትም በላይ የምህረት ጥግ ኢየሱስ ላይ ስለጣለው በነገው ሐሙስ አብሮት ሊበላ፣ እግሩንም ሊያጥበው አዘጋጅቶት ነበር።

መነሻ ሃሳብ ሕማማት መጽሐፍ
በዲያቆን ሄኖክ ኃይሌ

In Christ
Henok

02/14/2024

በአካሄድህ ማስተዋል በክህንነትህ ክርስቶስን አስብ
ምክር 4
2 ጢሞቴዎስ 2:2

"ብዙ ሰዎች የመሰከሩለትን ከእኔም የሰማኸውን ሌሎችን ደግሞ ሊያስተምሩ ለሚችሉ ለታመኑ ሰዎች አደራ ስጥ።"
እዚህ ጥቅስ ውስጥ አራት ቅብብሎሽ በትንሹ እናያለን።

እነርሱም
ብዙ የመሰከሩለት ( የቀደሙት አባቶች)
ከእኔ የሰማኸውን(ጳውሎስ)
ለታመኑ ሰዎች የሚያስተላልፈው (ጢሞቴዎስ)
ማስተማር የሚችሉ ታማኝ ሰዎች(ቀጣይ ትውልድ)

ከእነዚህ ውስጥ የትኛው ጋር አንተ አለህ? ጥሪያቸውን አሳክተው ከሚያስተላልፉት ወይስ ለመጀመር በታማኝነት ከሚቀበሉት። ወንጌል በባህሪው ክርስቶስ ዳግም እስኪመጣ ድረስ የሚቀጥል በመሆኑ ተረካካቢ ነው።

የተቀበልከው ካለ የሚቀብልህ ደግሞ አለ። ይህ የወንጌል አጠቃላይ ስሬት ነው። የጢሞቴዎስን ለየት የሚያደርገው ሁለት ነገር በአንድ ላይ መቀበሉ ነው። የኤፌሶንን ቤተክርስቲያን እና ወንጌሉን።

ከእርሱ በፊት የነበሩት ሐዋሪያት ወንጌልን በየደረሱበት ይዘው ይጓዙ ወይም ለተወሰነ ጊዜ በአንዳንድ ከተሞች ይቀመጡ ነበር። በእርግጥ አገልጋዬችን ለመሪነት ሲልኩ መሪም ሆነው ውሳኔ ሲሰጡ ታይተዋል። ለዘለቄታው ግን አንድ ቤተክርስቲያን ላይ በመሪነት ለማገልገል ሲመረጥ ይህ ልጅ የመጀመሪያ ነው። የመጋቢ መፅሃፍ መባሉም ከዚህ የተነሳ ነው።

ቤተክርስቲያን እና ወንጌል የሚለያዩ አይደሉም። ወንጌል ያለ ቤተክርስቲያን ሊቆም ይችል ይሆናል። ማናችንም ባንታመን እርሱ የታመነ ነው ስለሚል (2ጢሞ 2:13) በፍጹም ግን ቤተክርስቲያን ከወንጌል ውጪ አትዘልቅም።

ወንጌል ከእግዚአብሔር ሃሳብ ጋር የተገናኘንበትና የምንቀጥልበት ካህን የሆንበት መሰረታችን ነው። ከእርሱ ወደ እኛ የመጣ ሰማያዊ ሃሳብ vertical thought (priesthood) ቤተክርስቲያን ደግሞ ወደ ጎን እየሰፋች የምትሄድ ሁለትና ከዛ በላይ ሰዎች ያሉባት መለኮታዊ ተቋም ነች። Horizontal divine sector (Leadership)

ይች ተቋም በየእለት እለት ህይወት ውስጥ አለች። ቤት ውስጥ እንደ ቤተሰብ፣ ስራህ ቦታ እንደ ወዳጅነት ወይም የምትማርበት ስፍራ እንደህብረት ትገኛለች። የግድ እሁድ የምትሰባስባት ስፍራ ብቻ አይደለችም።

በዚህ ምዕራፍ አደራ የሚሰጠው ነገር ዘላቂ እንዲሆንና ኤፌሶንን ተሻጋሪ ለማድረግ የሚችልበትን የአመራር ልህቀት ወንጌሉን ማዕከል በማድረግ ማሳየት ነው።

ክፍሉን በደንብ ስናጠና የምናገኘው አገልግሎት የተሻለ ቁመና እንዲኖረው ዛሬ ላይ ምን ማድረግ እንዳለብን፣ ቀጣይነት ያለው ስራ ለተረካቢው እንዴት መስራት እንደሚቻል ምክር መስጠት ነው።

የተቀበልከውን በዚህ ልክ ለሚቀጥለው ለማሳለፍ እድሉ በእጅህ አለና ሁለቱን የሚያጣምርልህ ሃሳብ ከጳውሎስ እንካ. . .

"የምለውን ተመልከት፤ ጌታም በነገር ሁሉ ማስተዋልን ይስጥህ።" 2 ጢሞ 2:7 (Leadership)

"በወንጌል እንደምሰብከው፥ ከሙታን የተነሣውን፥ ከዳዊት ዘርም የሆነውን ኢየሱስ ክርስቶስን አስብ::" 2 ጢሞ 2:8 (preisthood)

ይኸውልህ ክህንነት እና አመራር በደንብ ሲጣመሩ ያስታውቃል ሳይጣመሩም እንዲሁ። ስለዚህ በአካሄድህ ማስተዋልን በክህንነትህ የክርስቶስን ወንጌል አስብ።

ማስተዋል

ማስተዋል በነገሮች መሃከል ሚዛንን እንድትጠብቅ የሚረዳህ የአዕምሮ ጥበብ ነው። ማስተዋል በነገሮች የበላይ እንድትሆን የሚያስችል አቅም የስኬትህ ባለውለታ ለነገም ህይወትህ መተማመኛህ ነው።
የምንም ነገር ቀጣይነት በማስተዋልህ ልክ ይለካል። በጥበብ የተሰራ ቤት በማስተዋል ይፀናል እንደሚል። ምሳ 24:3

ማስተዋል
- የትላንቱን ከነገው ጋር የምታገናኝበት ድልድይህ ነው።
- የምትፈልገውን ከሚያስፈልግህ የምትለይበት ነው።
- የውሳኔ ዓቅምን የምታሳድግበት ብልሃት ነው።
- ከተለያየ አቅጣጫ የምታይበት ብሌንህ ነው።
- ለመናገርም ዝም ለማለትም ጊዜን መምረጫህ ነው።
- ዋጋ መክፈል ያለብህን ቦታ ይመርጥልሃል።
- የሌላውን ባህል፣ ዕሴት፣ አስተሳሰብ እንድተረዳ ያግዝሃል።
- የተነገረውን ብቻ ሳይሆን የቀረውንም እንድትሰማ እድል ይሰጥሃል።
. . ይቀጥላል

In Christ
Henok Zewdie

02/01/2024
01/27/2024

". . . እንደ ምሕረቱና እንደ ቸርነቱም ብዛት ለእስራኤል ቤት የሰጠውን ትልቅ በጎነት አሳስባለሁ"። ኢሳይያስ 63:7

01/24/2024

. . . ምስጋናም ይብዛላችሁ። ቆላ 2:7

ከባለፈው የቀጠለምክር ፪  አሉታዊ ፍርሃትህን አስወግድ"እግዚአብሔር የኀይልና የፍቅር ራስንም የመግዛት መንፈስ እንጂ የፍርሃት መንፈስ አልሰጠንምና"       2ጢሞ 1:7ፍርሃት ምንድን ነውፍ...
01/12/2024

ከባለፈው የቀጠለ
ምክር ፪ አሉታዊ ፍርሃትህን አስወግድ

"እግዚአብሔር የኀይልና የፍቅር ራስንም የመግዛት መንፈስ እንጂ የፍርሃት መንፈስ አልሰጠንምና" 2ጢሞ 1:7

ፍርሃት ምንድን ነው
ፍርሃት በስሜት ህዋሳቶቻችን በኩል ወደ ነፍሳችን በሚደርስ መረጃ ምክንያት በሰው ላይ የሚመጣ የተዛባ ስሜት ነው። በአጭሩ የነፍስ አለመረጋጋት ልንለው እንችላለን። ይህንን ማንነት በአግባቡ ካልያዝከው በህይወት ላይ የሚያስከትለው ችግር ቀላል አይደለም። በሁሉ ሰው ላይ አይነቱ ይለያይ ይሆናል እንጂ ፍርሃት አለ፣ አንዳችን ከሌላችን የሚለየን የፍርሃት መጠኑና የምናስተናግድበት መንገድ ነው።

በጢሞቴዎስ ላይ የታየው የአቅም ማነስ ሳይሆን ውጪ ውን አግዝፎ የማየት ፍርሃት ነበር። ይህ ልጅ ኤፌሶንን የምታክል ትልቅ ቤተክርስቲያን ለማስተዳደር ሲታጭ ከእድሜው የሚመጣ፣ ቤተክርስቲያኗ ካለችበት ከተማ የሚመጣ ምናልባትም በአካባቢው ካሉት ምሁራን አንፃር እኔ እንዴት አድርጌ የሚል ፍርሃት ይዞት ነበር።

ይህ እራስህን በይበልጥ አዘጋጀተህ እንድትወጣ ከጠቀመህ መልካም ሊሆን ይችላል። ነገር ግን አይሆንልኝም ብሎ ካስቀመጠህ ክፉ ፍርሃት ነው።
ጳውሎስም ይህንን ተረድቶ ስለነበር በተሰጠው አቅም ላይ ብቻ እንዲያተኩር መክሮታል።

ፍርሃት ሁልግዜ ውጪያዊ ነው። ከምትሰማው፣ ከምታየውና አካባቢህ ከሚሆነው ወደ ውስጥህ የምታስገባው ክፉ ነገር ።

አንዳንድ ሰው ፍርሃት ገና ሊጀምረው፣ መረጃው ሊመጣ ሲል ያውቀዋል ምናልባት ለጥቂት ጊዜ በአይምሮ ውስጥ ሊመላለስበት ይችላል ግን ብዙም አያስተናግደውም። ወደ አምላኩ ወይም ወደ ሚያሸንፈው እውቀት ጠጋ ይላል። ይህ አይነቱ ሰው ለመምሰል ሲታገል አታገኘውም ውጪውን ሆኖት ይገጥመዋል። ጠንካራውንም ሰው ይመስላል

ሌላኛው ሰው ላይ ደግሞ ቆየት ላለ ጊዜ ያታግለዋል። ባይሆንልኝስ ...ባይሳካስ...ልጀምረው ይሆን እያለ በውስጥ ሙግት ይከርማል። በዚህ ምድብ ውስጥ ያለ ሰው ከውስጥ አቅሙ ይልቅ የውጪው ተግዳሮት ይገዝፍበታል። ተግዳሮትን እንደ መልካም አጋጣሚ ከተጠቀመ ወይም የውስጥ ሃይሉን በሙላት ከተረዳ ትልልቅ ነገር በማከናወን የሚታወቅ ምድብ ነው። አትፍራ..አይዞህ ቀጥል የሚባሉ ሰዎች በዚህ ምድብ ውስጥ ያሉ ናቸው።

እስከመጨረሻው ደግሞ አምኖት የሚያስተናግደውም አለ። ይህኛው ሰው ይገጥመኛል ብሎ የሚያስበው ነገር በውስጡ የሚፈጥርበት ፍርሃት በእጅጉ ይጎዳዋል። ይህን ፍርሃቱን ለመደበቅ ሲልም የሚወስዳቸው እርምጃዎች አደገኛ ሊሆኑ ይችላሉ። አንዳንዴም ፍርሃቱን ከማስወገድ ይልቅ በውጪ ጠንካራ ለመምሰል በሚያደርገው ትግል ውስጥ ራሱን ይደብቃል።

ብዙ ግዜ አዲስ ነገር ለመጀመር ታቅዶ የማይሳካው ወይም መስራት ያለብንን ሳንሰራ የምንቀረው ነገሩን ሞክረን አቅቶን ሳይሆን ሳንጀምረው እንደማይሳካ የሰበሰብነው ምክንያቶች ስለሚይዙን ነው። ጥንቃቄ እንዳትለኝ፣ በርግጥ መጠንቀቅ የሚያስፈልገን ቦታ እንዳለ ባምንም ብዙ ጊዜ ግን የሚይዘን ፍርሃት ነው። እነዚህን ምክንያቶች አሸንፎ መውጣት በራሱ ግማሽ መንገድ ነገሩን እንደማሳካት ነው።

ስለዚህ ግድ የለህም ራስህን ለመለወጥ በውስጥህ ያለውን እና የምትፈራውን ነገር ሞክር፣ የትላንት ህይወትህን በመደጋገም አትቁይ ድፈር። አእምሮህን አሸንፈህ ከወጣህ ውጪ ያለው በፍፁም አያቅትህም፣ የጀመርከውም ነገር መፈፀሙ አይቀርም።

ጳውሎስ ይህንን ልጅ ከገባበት ፍርሃት ለማውጣት የተጠቀመው ምክር "የፍርሃት መንፈስ" አልተሰጠህም የሚል ነው ለአንተም ይህ እውነት ነው።

ይልቁን በአሸናፊነት እንድትወጣ የሚረዳህ የኃይል መንፈስ፣ ሁኔታዎችን የምትይዝበት የፍቅር መንፈስ እንዲሁም በስሜትና እውቀትህ መካከል ሚዛን(balance) የሚጠብቅልህ የራስን መግዛት መንፈስ ተቀብለሃል።

ልጆች ሆይ፥ እናንተ ከእግዚአብሔር ናችሁ አሸንፋችኋቸውማል፥ በዓለም ካለው ይልቅ በእናንተ ያለው ታላቅ ነው።1 ዮሐንስ 4:4

In Christ
Henok

01/08/2024
01/05/2024

አንተ ግን...ቀጥል
ይህን ቃል ተደጋግሞ በምክር መልክ የምናገኘው በ2ኛ ጢሞቴዎስ መፅሐፍ ላይ ነው። ምክሩም አንድን በፍርሃት ውስጥ የሚገኝን ወጣት ለማበረታታት እና በሚበልጥ ክብር እንዲቀጥል ያበረታታበት የወዳጅነት እና የአስቀጣይነት ምክር ሆኖ እናገኘዋለን።

መፅሐፉ ጳውሎስ ከፃፋቸው የግል ደብዳቤ ውስጥ ሰፊ በመሆኑም ይታወቃል። በተለይ ህይወቱ ሊያልፍ ሲል የፃፈው መፅሃፍ እንደመሆኑ ያለውን ምክር ሁሉ የለገሰበት መፅሃፍ ነው ቢባል አያንሰውም።

ለመፃፍ ምን አነሳሳው? እኔስ ለምን መረጥኩት

፩. ሁኔታዎች አስቸጋሪ ሲመስሉህ፣ እያለህ እንደ ሌለህ ከተሰማክና አስቸጋሪ ሁኔታ መካከል ስትገኝ... አንተን ከሁኔታህ በላይ ማድረግ የሚችል ምክር ስላለበት።

፪. በእጅህ የተሰጠህን ነገር ላትፈፅመው ሲመስልህ፣ ምናልባትም የአቅም ጉዳይ አስጨንቆህ እና እነ እገሌ ያልቻሉትን እኔማ ማነኝ የሚል ስሜት ከተሰማህ

፫. ሄሜኔዎስ እና ፊሊጦሳውያን ጭቅጭቅ መንደር ውስጥ ስትገኝ፣ የጎልማሳነት ስሜት ውስጥህን ሲንደው ውጪውን ፈርተህ አቅምህ ሊከዳህ ካለ

፬. ምናልባት ስደት ሰልችቶህ፣ ሁኔታዎች በውስጥህ ቀስ በቀስ እየቀለሉብህ ከመጡ፣ በማወቅ እና አለማወቅ መካከል የሰጠምክ ከመሰለህ

፭. እነ ዴማስ ከአገልግሎት አለማዊነትን በፊትህ ሲመርጡ በቤቱ ውስጥ እጅግ ክፋት ቀልድና ነውር ሲበዛ አይተህ ምን ጉድ መጣ ብለህ እያሰብክ ካለህ 2ኛ ጢሞቴዎስን ልጋብዝህ ነው

እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ሁኔታዎች በወጣቱ አገልግሎት መስክ ላይ የተገኙ መሰናክሎች ነበሩ። ሐዋርያው ተግዳሮቶቹን ከወጣቱ አይምሮ ውስጥ አውጥቶ ወደ ተሰጠው ህልም ፊቱን እንዲመልስ እና ከልጅነቱ የደከመበትን ማፍሪያው ሰዓት ላይ ከንቱ እንዳይሆንበት የፃፈለት የግል ደብዳቤ ነው።

አንተም አሁን ላይ ያለ ስሜትህን ከላይ ከተዘረዘሩት ውስጥ ካገኘኸው ተከተለኝ።

በመፅሃፉ ላይ ወደ 17 የሚሆኑ ቀጥተኛ ምክሮች 5 ያህል ደግሞ ቀጥተኛ ባይሆኑም ነብስን የሚሞሉ ምክሮች እናገኛለን። ታዲያ በየትኛውም ዘመን ለምንገኝ አገልጋዮች እንዲጠቅሙ ሆነው የተሰናዱ ናቸው።

22 ምክር እንዳትል አይዞህ ሁሉኑም እዚህ አላመጣቸውም።

ለዛሬ ምክር 1 ብቻህን አይደለህም

2 ጢሞቴዎስ 1: 3
"ሌትና ቀን በልመናዬ ሳላቋርጥ ስለማስብህ እንደ አባቶቼ አድርጌ በንጹሕ ሕሊና የማመልከውን እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ"

በውጣ ውረድ ውስጥ ስታልፍ የሚረዳህና የሚያስብልህ እንዳለ ማሰብ። ስሜትህን የሚረዳህ ተስፋ በቆረጥክበት ሰአት አይዞህ የሚልህ ወገን ማግኘት፣ ያውም ሌትና ቀን ሳትቋርጥ መታሰብ እንዴት መታደል ነው።

ምናልባት ደፍሮ ስላንተ ይጨንቀኛል፣ አስባለው የት ነው ያለኸው የሚልህ አጠገብህ በጊዜው ላይኖር ይችላል። ግን በፍፁም ተስፋ አትቁረጥ ነገ እግዚአብሔር የነገረህ በእጅ ይሆናል።

ያዕቆብ ወንድሙን በመሸሽ ብቻውን ወደ ማያውቀው ምድረ በዳ ጉዞ በጀመረበት ሰአት ይህ ስሜት ተሰምቶታል ብዬ ባስብ ከሁኔታው ብዙ የራኩ አይመስለኝም። አስቡት በተከበረ ቤት ውስጥ ይኖር የነበረ ልጅ፣ ድንገት ራሱን ጭው ያለ ምድረ በዳ ላይ ሲያገኘው። ያውም የኪዳን ቃል ይዞ ....አንዳንዴ ህይወት እንዲህ ነው

መንገዱን አያውቀው፣ የሚሄድበትን ቤት አያውቀው፣ እስከ መቼም በዚህ ሁኔታ ውስጥ እንደሚሆንም አያውቀው ...ብቻ የሚያደክም ጉዞ።

ሆኖም " እኔ ከአንተ ጋር ነኝ፥ በምትሄድባትም መንገድ ሁሉ እጠብቅሃለሁ፥ ወደዚችም ምድር እመልስሃለሁ፤ የነገርሁህን ሁሉ እስካደርግልህ ድረስ አልተውህምና።” የሚል የታስበሃል ድምፅ ሲመጣ ጉልበት እንዴት አይታደስ። ዘፍጥረት 28:15

በዚህ በማይመች ጉዞ ውስጥ አብሮት የሚጓዝ ወዳጅ እንዳለው እንደማይተወውም እንደተረዳ፣ በእግዚአብሔር ታስቤያለውም ሲል "ቤቴል" እንዳለ፣ ብቻህን እንዳልሆንክና የሚያስብልህ እንዳለ የምታውቅበት ሳምንት ቤቴልህ ይሁንልህ።

ነገር ምንም ቢከብድ ብቻህን አይደለህም

In Christ
Henok

01/01/2024

ከሁሉ የሚበልጥ ሊቀ ካህን አለን። ነገርን ውብ ማድረግ ልማዱ የሆነ ጌታ በዚህ ማንነቱ አመቱን ያግኛችሁ። 2024
ከሁኔታችሁ ከፍ የምትሉበት
በአዲስ ራዕይ የምትጎበኙበት
ትጋታችሁ የሚታደስበት
ከተስፋ መቁረጥ የምትለያዩበት አመት ይሁን።

In Christ

01/18/2023

ቤተ ክርስቲያን

ቤተ ክርስቲያን ማለት ስብስብ፣ ጉባኤን ያማከለ መሰባሰብን የሚወክል ቃል ሲሆን ይህም ስብስብ ለአንድ አላማና ተልዕኮ የተዋጀ ህዝብ የሚገናኝበትና ለአምላካቸው መሰዋእት የሚያቀርቡበትን ቦታ ሁሉ የሚሸፍን ህብር ቃል ነው። ይህም ህዝብ ሰማያዊ ጥሪን የተቀበሉ (ዕብ3፡1) በክርስቶስ እየሱስ ሞትና ትንሳኤ በማመን ዳግመኛ የተወለዱ (ዮሐ3፡16) እና በስሙ የተዋጁ (ኤፌ1፡7) የጌታ ልጆች ስብስብ ነው።

ቤተ ክርስቲያን በእግዚአብሔር ህዝብነት፣ በኢየሱስ ክርስቶስ አካልና ሙላት እንዲሁም በአለም ላይ የተተወላትን ተልዕኮ ለመጨረስ የምትሰራ ሰማያዊ ውክልና ያላት መንፈሳዊ ቤት ናት። በብሉይ ኪዳን የመገናኛው ድንኳን(ዘፀ 27፡21) የምስክሩ ማደሪያ(ዘኁ1፡50) የእግዚአብሔር መቅደስ (ዘኁ19፡20) የእግዚአብሔር ቤት ይባል እንደነበረ በዚህ አዲስ ኪዳንም ህዝቡ ለእግዚአብሔር አላማና እርሱን ለማምለክ የሚሰባሰብቡት ስፍራን ያጠቃልላል።

ይህ ስብስብ ሰዎች በራሳቸው መነሳሳት ያቋቋሙት የራሳቸው ማኅበር ወይም ለአንድ ግብና ለተወሰነ አላማ በህብረት በመደራጀት የጀመሯት ተቋም አይደለችም። ይልቁን በአላማዋም ሆነ አቋሟ ፍፁም የተለየች፣ መገኛዋ ይህ አለም ቢሆንም ከዚህ አለም ፍጹም ያይደለች ሰማያዊ ውልደት ናት።(ዮሐ 17፡14)

ቤተ ክርስቲያን እንደ እግዚአብሔር ህዝብ

ከላይ እንዳየነው ባጠቃላይ ቤተ ክርስቲያን የአማኞች ስብስብ ናት። በመስቀል ላይ በተሰራው ስራ አምነው ይህንን ታላቅ እርቅ የተቀበሉና እንደገና በአባታቸው ጉያ መግባት የቻሉትን ልጆች ያጠቃለለች ነች። እነርሱም "ያመኑት" በሚል መጠሪያ የሚታወቁ ሲሆኑ ያላቸው ሁሉ የጋራ ሀብት እንደሆነ የሚያስቡ ባህሪያቸው እምነት፣ መንፈሳቸው የአንድነት፣ አካሄዳቸው የሰላም የሆነ የእርሱ ህዝቦች ተብለዋል።

አብርሃም ለሚያምኑት ሁሉ አባት የተባለው ልጅነት በእምነት በሚገኘው ጽድቅ ብቻ ስለሆነ ነው። እግዚአብሔር በአብርሃም ህዝብን መረጠ። ይህም ህዝብ እስራኤል የሚል መጠሪያ ተሰጥቶት ከብዙ ባርነት በኋላ ከግብጽ አወጣው እንደ ህዝብም የሚሰፍርበትን፣ የሚያመልክበትን ቦታ ሰጠው። ይህ ከባርነት የወጣ ህዝብ በብሉይ ኪዳን የእግዚአብሔር ምርጦች በመባል ይኖሩ እንደነበርና አምላካቸው እግዚአብሔርም መሐከላቸው እንደሚኖር ይመሰከርላቸው ነበር። 2ሳሙ 5፥2

በአዲሱ ኪዳንም ከዚህ አለም በክርስቶስ አምነው በመሸሽ ወደዚህ መንግሥት የፈለሱ ሁሉ በእግዚአብሔር ህዝብነት ይታወቃሉ። መጽሐፍም ሲናገር "ሕዝቤ ያልሆኑትን፣ ሕዝቤ ብዬ እጠራቸዋለሁ" ሮሜ 9፥25 ምንም ቀድሞ በደቀደቀ ጨለማ ይኖሩ የነበረ ቢሆንም አሁን ግን ወደ ሚደነቅ ብርሃን እንደወጡና የእርሱ የተመረጠ ትውልድ እንደሚሆኑ ይናገራል።

በብሉይ ኪዳን እስራኤልን ከግብጽ ሲወጣ የተናገራቸው "የካህናት መንግሥት የተቀደሰም ህዝብ ትሆኑኛላችሁ" ዘጸ 19፡5−6 የሚል ሲሆን ይኸው ድምጽ በአዲስ ኪዳን ከአለም ለተለዩት ህዝቦቹ ተሰጥቷል። የመንግሥቱ ካህናት እና የተቀደሰ ህዝብ የመሆን ጥሪ። እግዚአብሔርም ለመረጠው ህዝብ ባለሙሉ መብትና ጠባቂው እረኛ ነው።
ቤተ ክርስቲያን እንደ ክርስቶስ አካልና ሙላት (ኤፌ1፥23)

የቤተ ክርስቲያን ራስ ክርስቶስ ነው። የወደዳት እርሱ ነው፣ የሚያጸናትም ሆነ የሚያኖራት እርሱ ነው። ይህች ቤት በምድር ላይ አካሉ ሆና እንድትመላለስ እውቅና የሰጠ ጌታ ኢይሱስ ነው። ይህም ንጽህትና ሙሽራ ሆና እንደተዋበች፣ ጉድፍ ወይም የፊት መጨማደድ ወይም አንዳች እንከን ሳይገኝባት ቅድስትና ነውር አልባ ሆና ጌታዋን እንድትጠብቅ ያስፈልጋታል። ለዚህም እርሱን ልትታዘዘው በእርሱ ልትኖር ግድ ይላታል።

በሌላም በኩል ኢየሱስ ክርስቶስ በስማይም ሆነ በምድር ሁሉን በሁሉ የሚሞላ ነው። ምድር ሁሉ የእርሱ ነች። የመለኮት ሙላት ሁሉ በአካል በእርሱ ይኖራልና ተብሎ ይህ ሰማያዊ ሙላት በክርስቶስ በኩል እንደተገለጸና እኛም የገዥነትና የሥልጣን ሁሉ ራስ በሆነው በክርስቶስ ሙሉ ሆናችኋል ተብሎ እንደተነገረልን(ቆላ 2፥10) ይህ የእርሱ ሙላት በልጆቹ አማካኝነት በቤቱ በኩል እንዲታይ የተቀመጠች አካሉ ነች።

ይህ ማለት አካልነቷን በተሰራላት ሰራ ስታገኝ፣ ሙላትነቷን ግን የተቀበለችውን በተሰጣት መሰምር ላይ በመጓዝ የምታቆየው ነው። ይህም በእግዚአብሔር የተወደዳችሁና ቅዱሳን ለመሆን ለተጠራችሁ የሚለውን ሐሳብ የያዘ ነው። በምድር ላይ ስላለች ግን በስመ አካልነት የራሷን መንገድ ቀይሳ ልትንቀሳቀስ ትችል ይሆናል። ያኔ ታዲያ አንዴ የተሰጣት አካልነት ከእርሷ ውስጥ ባይጠፋም የተመደበላት ሙላት ግን ፈጽሞ ልታመጣው አትችልም።

ስለዚህ ይህ ሙላት በቅድስና በመጓዝ የሚቀጥል፣ ለዘላለም ሕይወት በሚመጥን ኑሮ የተገነባ እና በክብርና ሽልማት የሚጠናቅቅ የህይወት ጉዞ ነው። ይህም በምድር ላይ ተሰሚነትን የምታገኝበት ዋናው መስመሯ ሲሆን፣ ከሌሎች ምድራዊ ተቋማትም የምትለይበት ሰማያዊ ባህሏ ነው።

ሌላው ሙላትነቷ ምስጢርን ገላጭ መሆኗ ነው። በቤተ ክርስቲያን እና በክርስቶስ መካከል ያለው ግንኙነት ታላቅ ሚስጥር ነው። ይህንን የቀደመ በእግዚአብሔር ዘንድ የነበረ ምስጢር በዚህ ዘመን ለአለም ሁሉ ለመግለጥ የሚጠቀምባት የእግዚአብሔር ብቸኛ ልሳን ቤተ ክርስቲያን ነች። ለዚህም "ለእናንተ የእግዚአብሔርን መንግሥት ምሥጢር ማወቅ ተሰጥቶአችኋል. . ." ማር 4፥11 ተብሎ የተነገረላት።

ከእነዚህ ምስጢራት መካከል የሰው ልጅ ዳግም የመወለድ ምስጢር፣ የመስቀሉ ስራ፣የመነጠቅ ምስጢር፣ የቅዱሣን ትንሳኤና ሙታን የማይበሰብሱ ሆነው መነሣታቸው፣ የሐሰተኛው ክርስቶስ ምስጢር የመሳሰሉት በአለም ዘንድ እንደቀልድ የሚታዩት ወይም የማይታውቁት ምስጢራት በቤተ ክርስቲያን በኩል ግን እምነቷና የህይወቷ መርህ ሆነው ያቆይዋታል።

In Christ
ሄኖክ ዘውዴ

01/18/2023

የካህናት ተግዳሮት
ከባለፈው የቀጠለ
በዚህ አገልግሎት ላይ አንዳንድ ማንነታቸውን ያልለወጡ ካህናት በአገልግሎቱ ላይ ተጽዕኖ ሊፈጥሩ ቢሞክሩም እግዚአብሔር ግን አስፈላጊውን ቅጣት እየሰጠ ሕዝቡን እና ቤቱን በመጠበቅ እንዲጓዙ ያደርግ ነበር። በጉዞው ላይም ከታዩት ችግሮች ውስጥ ዛሬም ድረስ ለአገልግሎት እንቅፋት የሆኑትን በመምረጥ ለማየት እንሞክር።

1. ለብቃት ያለመኖር

የእግዚአብሔርን ቤት የሚያገለግለው ካህን ወይም ሌዋውያን ሁሉም በሌዊ የዘር ሀረግ ውስጥ መገኘት እንዳለባቸውና ለመቆጠር ከአንድ ወር ጀምሮ እንደሚችል የታወቀ ቢሆንም ለማንኛውም አገልግሎት በቂ የሚሆነው ግን እድሜው ሠላሳ አመት እና ከእዚያ በላይ ሲሆን ብቻ ነበር። ከዚህ ዘር መወለዱ ለቤቱ አገልጋይነት ሙሉ ፍቃድ ይሰጠዋል ሙሉ እድሜ ላይ መሆኑ ደግሞ በአገልግሎቱ የሚገጥሙትን የጉልበትም ሆነ ስነ ልቦናዊ ጉዳት እንዲሽከም አቅም ይሆነዋል።

ስለዚህ በመወለድ ያገኘውን አገልግሎት ከአባቶቹ በመማር ወደ ብቃት ማድረስ ተገቢ ነበር። ስለዚህ ከቀን ውሎው ጀምሮ ከሚመስለው ጋር በመሆን የሚማረው ሁሉ ስለ አገልግሎቱ ብቻ ነበር። መዳን በጸጋ ሲሆን ክህነት ግን በእውቀት የሚሆን ነው።

ኢየሱስም በምድር ላይ ባሳለፈው የሰላሳ ሶስት አመት እድሜው ውስጥ የመጀመሪያው የተናገረውና ሕይወቱን አሳልፎ ሊስጥ ባለበት በመጨረሻው ሰአት የተናገረው ይህንን የመጣበትን አላማ በማሳወቅ ነው። በአስራ ሁለት አመቱ በአባቱ ቤት ሊገኝ እንደሚገባው በማሳወቅ ሊፈልጉት ለመጡት ቤተሰቦቹ ሲናገር ይህ ንግግር በመጽሐፍ ቅዱሳችን ውስጥ የኢየሱስ የመጀመሪያው ንግግር ነው። "ለምን ፈለጋችሁኝ? በአባቴ ቤት መገኘት እንደሚገባኝ አላወቃችሁምን? ሲላቸው፣ በዮሐ 17 ላይ በታላቁ ጸሎት ጊዜ ደግሞ "የሰጠኽኝን ሥራ በመፈጸም በምድር አከበርሁህ በማለት" የምድር ቆይታውን ባጠቃላይ የተላከበትን በማድረግ ሊቀ ክህነቱ ላይ እንዳሳለፈው አሳይቷል።

ለዚህም ትልቅ ብቃት ይሆነው የነበረው ከእግዚአብሔር በአላማ መወለዱ እና በእግዚአብሔርም ሆነ በሰው ፊት በሞገስና በጥበብ ማደጉ ሲሆን፣ የየእለት ህይወቱም ከተላከበት አላማ ጋር ብቻ ማዋሀድ መቻሉም የሚጠቀስ ነው። ዮሐ 4፥34 ኢየሱስም እንዲህ አላቸው "የእኔ ምግብ የላከኝን ፈቃድ ማድረግና ሥራውንም መፈጸም ነው።

ሐዋሪያው ጳውሎስም ዳግም የተወለደበትን ሐሳብ ጠቅልሎ ሲያስቀምጠው እንዲህ ይላል፤ "ይህን ሁሉ አግኝቻለሁ ወይም ፍጹም ሆኛለሁ ማለት አይደለም፤ ነገር ግን ክርስቶስ ኢየሱስ እኔን የእራሱ ያደረገበትን ያንን እኔም የራሴ ለማድረግ እጣጣራለሁ" ፊል 3፥12 ይህ ሰው ጌታ ለምን እንደፈለገው በአንደበቱ
ሲናገር ". . . ሂድ፤ በሩቅ ወዳሉት አሕዛብ እልክሃለሁና" አለኝ ብሏል። በህይወቱ ቆይታውም ይህንን ጥሪ የራሱ በማድረግ ለመፈጸም ሩቅ ጉዞ ሲያደርግ፣ አባቶችን ሲጠይቅ እና ከቀደሙት ሲማር ታይቷል። (ገላ 2፥2)

ለክህንነት ስራ መወለድ አስፈላጊ እንደሆነ ሁሉ ስለተወለድንበት አላማ ያለን እውቀትም በጣም አስፈላጊ ነው። "ካህኑ የሁሉ ገዥ፣ የእግዚአብሔር መልእክተኛ ስለሆነ ከንፈሮቹ ዕውቀትን ሊጠብቁ፣ ሰዎችም ከአንደበቱ ትምህርትን ሊፈልጉ ይገባል።" ሚል 2፥7 እግዚአብሔር ለሌዋውያን በብሉይ ኪዳን የማገልገያ ጊዜ እንዳስቀመጠ ሁሉ ለእኛም ወቅትን መድቦልናል። አንዳንድ ጊዜ ከወቅታችን ቀድመን በመነሳት ወይም በጣም በመዝገየት የተሰጠንን ሐላፊነት በሙላት ለመወጣት ሲታክተን ይታያል።

በጊዜያችንም ልንጠቀም ስንችል በተለያየ ምክንያት ከሐሳባችን ዞር እያልን ጊዜውን የምናቃጥል፣ ከጊዜው የተነሳ አስተማሪዎች መሆን ሲገባን ገና ባለማደግ ውስጥ የምንዳክር ወይም ደግሞ ብቁ ሆነን ሳለን በፍርሐት ውስጥ የምንመላለስ ስንቶች ነን።

በእርግጥ የቤተ ክርስቲያን አንዱ ስራ ሰዎችን ለአገልግሎት የበቁ ማድረግ ቢሆንም ለዚህ ጉዳይ ከእራሳችን ውጪ ግን ማንንም ተጠያቂ ልናደርግ አንችልም።
"ነገር ግን በጌታችንና በአዳኛችን በኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና እውቀት እደጉ" 2ኛ ጴጥ 3፥18

2. ያልተሰጠንን መፈለግ

ለሁላችን እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ እርሱ እንደወደደው ጸጋውን አካፍሏል። ማንኛውም የአገልግሎት በረከታችን ያለው በእዚህ በተሰጠን ጸጋ ላይ ነው። ሰዎች በፍላጎታቸው ጸጋዎችን ቢያበላልጡም ሁሉም ጸጋዎች ቤቱን የሚጠቅሙ፣ ቅዱሳንን የሚያነቁ እንደሆነ መገንዘብ አለብን። የቀዓት ልጅ የሆነው ቆሬ ከሌዋውያን ወገን አንዱ ሲሆን በመገናኛው ድንኳን ውስጥ በመግባት ንዋየ ቅዱሳቱን በመጠበቅና መገናኛው ድንኳን ከሰፈሩ ለመነሳት ሲዘጋጅ በአሮን እና ልጆቹ የተሸፈነውን መገልገያ ለመሸከም የሚመጣ ነበር። ዘኊ 4፥15 " አሮንና ልጆቹ መቅደሱንና ዕቃዎቹን ንዋየ ቅዱሳቱንም በሙሉ ሸፍነው ከጨረሱ በኋላ ሰፈሩ ለመንቀሳቀስ ዝግጁ ሲሆን፣ ቀዓታዊያን ለመሽከም ይምጡ"

ሆኖም ግን ከሮቤል ነገድ ልጆች ጋር ሆኖ ሰዎችን ለክፋት በማስተባበር በሙሴ እና በካህኑ አሮን ላይ ተቃውሞ አነሳሳ። የተቃውሞውም መሪ ሐሳብ ከተሰጣቸው አገልግሎት በላይ የክህንነቱን ስራ ደርቦ ለመስራት አቅሙ አለን የሚል ነው። ሁላችንም የሌዊ ልጆች ነን እናንተን ብቻ የቤተ መቅደሱን ሙላዊ አገልግሎት መያዝ አይገባችሁም ለእኛም የሚሆን ስፍራ ያስፈልገናል ሁልግዜ በሽክም ብቻ አለቅን የሚል አይነት ነበር። በእርግጥ ከእግዚአብሔር የተሰጠህ እስከሆነ ድርስ በሸክምም ይሁን በማጠን ቤቱን ማገልገል ለእግዚአብሔርም ሆነ ለህዝቡ ያለው ጠቀሜታ እኩል ነው።

የሰው ሁሉ ችግር በተሰጠው ነገር ሳይሆን ለአይን ታይታ በሚስብ ቦታ ላይ ማገልገል መፈለጉ ነው። ዛሬ በሚያሳዝን መልኩ ወንጌል ወጥቶ መስበክ ያለፈበት እየመሰለ፣ በመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ውስጥ በመመማርና ማስተማር ሂደት ውስጥ መካፈል የልጆች ስራ እየመሰለ፣ በጸሎት አገልግሎት መታቀፍ ማንም የማያየው የጓዳ አገልግሎት ስለሆነ በሰው መመናመን እየተጎዳ በአጠቃላይ ቤቱ በሙሉነት እንዳይንቀሳቀስ የእራሳችንን አስተዋጽኦ እያረግን እንገኛለን።

ይህንንም ተገን በማድረግ ሰዎች ሁልጊዜ ከምዕመን ያለፈ ተግባር እንደሌላቸው የሚያስቡ መሪዎችም በጣት የሚቆጠሩ አይደሉም። ካልሞቱ በስተቀር ቦታውን ማስነካት የማይፈልጉ፣ እነርሱ ጠቅልለው ከሚያጎርሱት ውጪ ሌላው ምግብ ሁሉ የተበላሸ የሚመስላቸው፣ ልጄ አደገልኝ ሳይሆን አደገብኝ የሚሉ ብዙዎች ናቸው። ይህም ቤቱን በተሻለ እንዳይንቀሳቀስ ከማድረጉም በላይ የህዝበ ክርስቲያኑን መንፈሳዊ እድገትም እንዲቀጭጭ አድርጓል። ይህ ሁለት የየራስ አመለካከት በማህበረሰባችን ውስጥ ዳርና ዳር በመጓተት ወርቃማ ጊዜ ያለምንም የተሻለ ውጤት ለማለፍ ትልቅ ምክንያት ሆኗል።

በእርግጥ ህዝበ ክርስቲያኑ መቶ ከመገልገል ውጪ የሚጠበቅበት ያለፈ ተልዕኮ እንዳለው ያወቀም አይመስልም። በቤቱ ውስጥ አስርና ሀያ አመት መቀመጪያ ስፍራቸውን እንኳን ሳይቀይሩ በአንድ ቦታ ላይ ሆነው የመርዶኪዮስን ታሪክ መጽናኛ አድርገው አንድ ቀን ንጉሱ ያስበኛል የሚሉ ብዙ፣ በጣም ብዙ ናቸው። እንደምናውቀው መርዶክዮስም ቢሆን በባቢሎን በስደት ምድር ላይ አይሁዲነቷን ጠብቃ በማንነቷ እንድታድግ ያስቻላት አስቴር የምትባል ለአይሁድ መዳን ምክንያት የሆነችን ሴት አሳድጎ አበርክቷል። ስለዚህ ባለህበት ዘመን ምንም ያህል ትንሽ ትሁን ለመንግስቱ ስራ አደራ አለብህ።

3. ፅናት ማጣት

ክህንነት ጠላት ክፉኛ የሚያጠቃው አገልግሎት ነው። ብዙ ድካምም ይጠይቃል አንዳንዴ በጸጋው ላይ ያለን እምነት የጠነከረ ስለሆነ እንጂ የሚቻል አይደለም። ለዚህ አገልግሎት እግዚአብሔር ለእነርሱ ብቻ ለይቶ የሰጣቸውና ከማንኛውም ህዝብ የሚለዩበት እንዲሁም በምድሪቷ ላይ የእግዚአብሔር ተወካዮች መሆናቸው የሚታዩበት የተለየ ክብር ነበራቸው።

ከዚህም ክብር ውስጥ አንዱ ልብሳቸው ነበር። ይህ ልብስ በታወቁ ጥበበኞች የተሰራ ብቻ ሳይሆን አጠቃላይ ንድፉ የእግዚአብሔር ነው። ይህ ካህኑ ብቻ የሚለብሰው በጨለማው አለም ላይ ብርሃን እንዳለ፣ እግዚአብሔር እንዳልተዋቸው የሚመለከቱበት ልብስ ነበር። ካህኑ ልብሱን ለብሶ ሲመጣ በላዩ ላይ ባለው ክብርና ሞገስ የተነሳ አምላካቸው ምንኛ የተዋበ እንደሆነ ከማሳየቱም በላይ፡ ይህንን ልብስ ለመልበስ የታደለው ካህን ምንኛ በአምላኩ ዘንድ የተመረጠ እንደሆነ የሚያሳይ ነበር።

ሰዎች እንደአካባቢያቸው፣ ባህላቸው፣ እምነታቸውና ባሉበት ስፍራ ባለው አየር ንብረት መሰረት ሁሉም የየራሱ መለያ ያለው አለባበስ ይጠቀማል፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ልብስ ዘመንን፣ ስልጣንን፣ እውቀትንና ውበትን መገለጫም ሆኖ ያገለግላል። አሁን አሁን አልባሳት ትልቁን የአለም የንግድ ክፍል የተቆጣጠረ ሲሆን የሰዎችም የኑሮ ደረጃ መለኪያ ሆኗል። አለም ወደ አንድ መንደር በመለወጥ ላይ ስላለች የአለባበስም አይነት መወራረስና አንዱ የአንዱን በመከተል በሁሉም ዘንድ አንድ የሆነ የአለበበስ ስርአትን መመልከት የተለመደ ነው።

ሆኖም ግን ለካህናት በብሉይ ኪዳንም እንኳን ሊለብሱት የተሰጣቸው ልብስ ክብርን፣ ውበትን ዝናን ሁሉ አጠቃሎ የያዘ ሲሆን ማንም እንደፈለገው የሚለብሰው አይነት ልብስም አልነበረም።

01/18/2023

የጊዜ ጠላቶች

1. ጊዜ እንዳለን ማሰብ፡−
ጊዜ ዞሮ የሚመለሰው ግርግዳ ከሰቀልነው ሰዓት ላይ ብቻ ነው። ሰአቶቻችን ይህን ሊያስታውሱን ይገባል። ጊዜ የለም ልትሰራው በልብህ ያለ ነገር ካለ ተነስና አድርገው። ታውቃለህ ትልቁ ሰአትህን የሚወስደው ምን እንደሆነ፤ ልትሰራው የምትፈልገውን ነገር እስክትጀምረው ድረስ የምታቃጥለው ጊዜ ነው። ገና ነው፣ ምንችግር አለው ትደርሳለህ፣ ዋናው መድረሱ እንጂ በስንት ሰአት መድረስህ አይደለም የሚባሉት የህዝባችን አባባሎች ሁልጊዜ በጊዜ መትረፍረፍ ውስጥ የምንኖር አስመስለውናል። እውነታው ግን ጊዜያችንን እያጠፉት ነው። The most trouble thing in time is, you think you have more time. ከቡድሀ አባባሎች ውስጥ አንዱ።


2. በተሳሳተ መንገድ መጓዝ (Misdirection)፡−እረጅም ከተጓዙ በኋላ መንቃትን የሚያህል የሚያናድድ ነገር የለም። በርግጥ ከሚቀጥለው ኪሎ ሜትር በፊት መንቃትና መመልስ የተሻለ ቢሆንም። መንገድ ከመጀመሩ በፊት ሁሉን መጠየቅና በማወቅ እንደመጀመር ትርፋማነት ያለው አይደለም። አንዳንድ ሰው ከዘመናት በፊት ይህን ባደርግ ኖሮ እያለ አሁን ያለበትን የህይወት ሩጫ ይገታዋል። አንዳንዱ ደግሞ የትላንት ስህተቱን ለማካካስ በሚመስል ሌላ የስህተት ጎዳና ይጀምራል። ሌላው ደግሞ ብዙ ነገሮችን ለመስራት በብዙ ቦታ ይባክናል በመጨረሻ ሁሉም ጅማሬ ብቻ ይሆንበትና አንዱንም ሳይጨርስ ይደክማል። እነዚህ ሁሉ የተሳሳቱ መንገዶች ናቸው። ከታዘብኩት ውጤታማ የሚያደርግህ አንድ ነገር ለመስራት መነሳትህ እና የምትጓዝበትን መንገድህ መምረጡ ላይ ነው።

3. ግብ የለሽ ህይወት፡

ማለት የምትኖርለት አላማ ያለመኖር፣ በህይወትህ ግብህ ምንድነው?የቱንም ያህል ትንሽ ሊመስል ይችላል ሆኖም ግን ለይተህ ታውቀዋለህ ወይ። ግብህንስ ለማሳካት የቀየስከው መንገድ አለ ወይ? እንደምትጨርሰውስ ምን ያህል እርግጠኛ ነህ? እያንዳንዱ ሰከንድ ለአላማህ ወሳኝ እንደሆነስ አስበህ ታውቃለህ? ከተሰጡህ 24 ሰአት ውስጥ ለአላማህ ምን ያህሉን ታውላለህ . . .

ዕቃ ለመግዛት ሃያ ብር ኖት ይዘን ብንገበያይ እና ከገዛነው ላይ ሁለት ብር ቢመለስልን የተመለስልንን ትንሽ ገንዘብ ለሌላ አላማ እንደምንጠቀምበት (እንደማንጥላት) ሁሉ በቀን ውስጥ ሁሉን አድርገህ የሚተርፍህን አንድ እና ሁለት ሰአት ለምን ያለምንም ውጤት አልባሌ ቦታ ትጥለዋለህ. . . እነዚህ ጥያቄዎች እንዴትና ወዴት መሮጥ እንዳለብህ ያሳይሃል።

ግብ ህይወትህን በብዙ መንገድ ይጠቅመዋል

የህይወት ግብ ካለህ የምትሮትበት አላማ አለህ
የህይወት ግብ ካለህ የተቃና እይታ ይኖርሃል
የህይወት ግብ ካለህ ሁሌ መነቃቃት ይታይብሀል
የህይወት ግብ ካለህ ለመወሰን አትቸገርም . . . ግብ የለሽ ህይወት ስንፍናን (Laziness) ድብርትን (depression) ያስከትላል።(God is not disorganized- why are you?

4. አፍቅሮተ ስክሪን (Entertainment‚ phone‚ tv . . . )

አንድ ወዳጄ ስለ ኢንተርኔት ሲያጫውተኝ አልገባንም እንጂ ስሙ እራሱ መረብ ውስጥ መያዝ (inter−net) ነው ያለኝ አይረሳኝም። ድሮ ድሮ ሐብታሙ ብቻ ነበር ለመዝናናት የተፈጠረ የሚመስለው አሁን ግን በየትኛውም የኑሮ ደረጃ ላይ ያለ ሰው ኪሱ ውስጥ ይዟት በሚዞረው የህልም አለም፤ (ስልክን ማለቴ ነው)የፈለገበት በክሊክ (click) እየተጓዘ፤ የተጠራበትን እውነተኛ ህይወት የማይኖርበት ያህል እየመሰለ ያለበት ወቅት ነው። ያለ አግባብ ለሰአታት በሚዲያ ላይ ማሳለፍ ሰአትን መዋጀት ሳይሆን ሰአትን መግደል ነው። ይህን ስል ህዝባችን ሶሻል ሚዲያውን በብዛት ለምን አላማ እየተጠቀመው እንዳለ ስለሚታወቅ ነው። አባባሉ እራሱ ጊዜ ማሳለፊያ አይደል የሚባለው። በአግባቡ እና ለነገ ማንነት ገንቢ የሆነውን እየመረጥን የምንመገብ ከሆነ ዘመን ባመጣው መሳሪያ እየተጠቀሙ ከዘመኑ ጋር መፍሰስን የመሰለ ነገር የለም።

In Christ
ሄኖክ ዘውዴ

11/28/2022

እግዚአብሔር መልካም ነው

Address

Calgary, AB
T2C3R6

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when In Christ posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Videos

Share

Nearby media companies