30/10/2023
አዲሱን ትውልድ መረዳት!!
የአዲሲቷ ኢትዮጵያ ዋነኛ ባለቤት የሆነው የመደመር ትውልድ ከቀደሙ ትውልዶች የተለየ እንደሚሆን እሙን ነው፡፡ የመደመር ዘመኗ ኢትዮጵያ ኀብረ ብሔራዊ አንድነት ያለባት፤ የወንድማማችነት እሴት የፀናባት፣ የሲቪክ ባህል የጎለበተባትና ቀጣናዊ ትሥሥር የጠነከረባት ትሆናለች፡፡
ኀብረ ብሔራዊ አንድነቷ እውነተኛ ፌደራሊዝምን ተግባሪ፤ ብዝኃ ማንነትን አቃፊና ብዝኃ ልሳንን አስተናጋጅ ይሆናል፡፡ ሌላውን እንደራሱ የሚመለከት፤ ብሔሩንና ሀገራዊ ብሔረተኝነትን ያስታረቀ፤ የትናንቱን በጎ ነገር ይዞ የትናንቱን ሥህተት የሚያርም፤ትናንትን ከዛሬና ከነገ የስማማ፤በእነዚህ ጉዳዮች የልሂቃንን ስምምነት በማምጣት፤ ሀገራዊ መግባባትና ዕርቅን የሚያሰፍን ትውልድ ይፈጠርባታል፡፡
በስምምነትና በመግባባት የጋራና አስታራቂ ሕጎችን በመፍጠር የሚገነቡ ተቋማት፤ሰላሟንና ብልጽግናዋን ያረጋግጡላታል፡፡
የጎረቤቶቿን ሰላምና ዕድገት እንደ ራስዋ የምትመለከት፤ በጋራ ለማደግ ያለመ አካሄድን የምትከተል፤በንግድና በሌሎች ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች ለመተሳሰር የምትሻ፤ ቀጣናዊና አህጉራዊ ግንኙነቶቿን በመደመር መርሕ የምትመራ ሀገር ትሆናለች፡፡
የመደመር ትውልድ ገጽ 155