19/05/2023
ደሴ ከተማ
ከአዲስ አበባ 401 ኪ/ሜ ከባሕር ዳር 481 ኪ/ሜ ርቀት ላይ የምትገኘው የደሴ ከተማ ካላት ወታደራዊ ጠቀሜታ በተጨማሪ ተስማሚ የአየር ፀባይ፣ ማራኪ የተፈጥሮ ውበትና ልምላሜ የታደለች ሆና በመገኘቷ ለረጅም ዓመታት ለወሎ ባላባቶች መቀመጫ በመሆን ስታገለግል የቆየች ታሪካዊ ከተማ ናት፡፡
ውበትን ሁሉ የታደለችው የጥንቷ ላኮመልዛ የአሁኗ ደሴ አሁን ያላትን ቅርጽ በመያዝ በከተማነት የተቆረቆረችው ደግሞ በ1885ዓ.ም በወሎው ንጉሥ ሚካኤል (ፊት ሙሃመድ አሊ) ነው፡፡
ደሴ ከባህር ወለል በላይ በአማካኝ 2500 ሜትር ከፍታ ላይ የምትገኝ ስትሆን በስተምዕራብ ዙሪያዋን ማራኪው የጦሳ ተራራ ይከባታል፡፡ የጦሳ ተራራ የደሴ ከተማን ከቅርብ ርቀት ወደታች ለመመልከት እጅግ ተስማሚ ቦታ ነው፡፡ ቀደም ባሉ ዓመታት ከተማዋ የወሎ ጠቅላይ ግዛት ዋና ከተማ የነበረች ሲሆን አሁን ደግሞ የደቡብ ወሎ ዞን እና የደሴ ሪጅዮፖሊታንት ከተማ አስተዳደር መቀመጫ ናት።
ደሴ ከተማን ከስምንት አቅጣጫ ማለትም ከመንበረ ፀሐይ፣ ፊት በር ፣ አሳማው ሜዳ፣ ደንበልቄ፣ አራዳ፣ አይጠየፍ እና መድኃኒዓለም አካባቢ ያላት ውብ መልክ ይሄን ይመስላል፡፡
📷 Ashu Habesha