10/11/2022
"በላባቸው ከራሳቸው አልፎ ሀገርን ለማበልፀግ ለሚተጉ ዜጎች ላቅ ያለ ክብር አለን !!" - አቶ መለሰ ዓለሙ
የብልፅግና ፓርቲ አዲስ አበባ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ መለሰ ዓለሙ በጉለሌና በየካ ክ/ከተሞች በተለያዩ የስራ መስኮች የተሰማሩ ኢንተርፕራይዞችን የስራ እንቅስቃሴ ጎብኝተዋል።
በስራ ትጋታቸው ላባቸውን ጠብ አድርገው ራሳቸውን እና ቤተሰባቸውን በመለወጥ፤ ከተማዋን እና ሀገራችንን ለማበልፀግ እየተጉ ለሚገኙ ዜጎች ላቅ ያለ ክብር አለን ያሉት አቶ መለሰ ስራዎቻቸውን በማስፋት ተጨማሪ የስራ ዕድሎችን እንዲፈጥሩ አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ እንደሚገባ አስረድተዋል።
የሚሰራን ሰው ማበረታታ እና መደገፍ የሁሉም ኃላፊነት መሆኑን የገለፁት ኃላፊው በየደረጃው የሚገኘው መዋቅራችን የመልካም አስተዳደር፣ የአገልግሎት አሰጣጥና የአሰራር ማነቆዎችን በመቅረፍ የያዝነውን የብልፅግና ጉዞ ማፍጠን እንደሚገባ መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
በጉለሌ ክ/ከተማ የሚገኝ የመልሶ መጠቀም ማህበር ፕላስቲክና ሌሎች የወዳደቁ ቆሻሻዎችን በማሰባሰብ ለተለያዩ ቁሳቁሶች መስሪያ በማዋል ለከተማዋ ፅዳትም የድርሻውን እያበረከተ እንደሚገኝ በጉብኝቱ ተገልጿል።
በተጨማሪም በየካ ክፍለ ከተማ የሚገኝ የእንስሳት መኖ ማቀነባበሪያ ማህበር ለተለያዩ እንሰሳት መኖዎችን በማቀነባበር ለሌማታችን መትረፍረፍ የድርሻውን ጥረት እያደረገ ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ የመኖ ማቀነባበሪያን ጨምሮ ሌሎች ማሽኖችን በማምረት ለከተማችን የተለያዩ ድርጅቶችና ለተለያዩ ከተሞች ተደራሽ እያደረጉ የሚገኙ ወጣቶች የስራ እንቅስቃሴም ተጎብኝቷል።
በክፍለ ከተማው በኮምፖስ ምርት የተሰማሩ ወጣቶችን የስራ እንቅስቃሴ አቶ መለሰ በጎበኙበት እንደተናገሩት አመራሩ ከጎናቸው መሆኑን በማረጋገጥ ዛሬ የተከናወነው ጉብኝት ከተማችን ያሏትን አቅሞች ለማስተባበርና የተሻለ ሀሳብ ያላቸውን ዜጎች በማበረታታት ለሌማታችን መትረፍረፍ የድርሻቸውን እንዲወጡ ለማስቻል መሆኑ ገልጸዋል።