13/06/2024
የሀረር ኢኮ ፓርክ ግንባታ ስራ 92 በመቶ ተጠናቋል- አቶ ተወለዳ አብዶሽ
በሀረር ከተማ እየተገነባ የሚገኝው የሀረር ኢኮ ፓርክ ግንባታ 92 በመቶ መጠናቀቁን የሀረሪ ክልል ባህል ፣ቅርስና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አቶ ተወለዳ አብዶሽ ገለፁ፡፡
ከኢፌዴሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ የመደመር ትውልድ መፅሃፍ ሽያጭ በተገኘ ገቢ እየተገነባ የሚገኘው የሀረር ኢኮ ፓርክ ግንባታ አሁን ላይ 92 በመቶ ተጠናቋል።
ፕሮጀክቱ በአጭር ግዜ ውስጥ ለማጠናቀቅ በርብርብ እየተሰራ መሆኑን አብራርተዋል።
ፓርኩ በውስጡ ሀረር የምትታወቅበትን የጅብ ትርኢት ማሳያ አንፊ ቲያትር ጨምሮ የተለያዩ ባህላዊ የእደ ጥበብ ውጤቶች ለቱሪስቶች የሚሸጡበት ማእከላት እና የመዝናኛ ስፍራዎችን በውስጡ የያዘ መሆኑን ገልፀዋል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ ፓርኩ ሀረር እራሱን የቻለ የጅብ ትርኢት የቱሪዝም መዳረሻ እንዲኖራት የሚያስችል መሆኑን ገልፀዋል፡፡
ፓርኩ እየተገነባበት የሚገኘው ስፍራ ሀረር የምትታወቅባቸው የተለያዩ እፅዋት የነበሩበት ስፍራ መሆኑን አስታውሰው ቀደም ሲል በስፍራው ይገኙ የነበሩ አትክልት እና ቡናን ጨምሮ የተለያዩ መድሃኒትነት ያላቸው እፅዋቶችን በስፍራው መልሶ በማልማት ተጨማሪ የቱሪዝም መዳረሻ ለመፍጠር እየተሰራ እንደሚገኝም ገልፀዋል፡፡
ፕሮጀክቱ በጠቅላይ ሚኒስትር ዶክተር አብይ አህመድ ከተፃፈው የመደመር ትውልድ መፅሃፍ ሽያጭ በተገኘ ከ70 ሚሊየን ብር በላይ ገቢ በክልሉ የሚገኙ ባለሃብቶች የንግዱ ማህበረሰብ የመንግስት ሰራተኞች እና የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች ተሳትፎ እየተገነባ እንደሚገኝም ገልፀዋል፡፡
ፓርኩን ለመገንባት ከሚያስፈልገው 162 ሚሊየን ብር ከ50 በመቶ በላይ የሚሆነው የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍሎች የተሸፈነ መሆኑ ፕሮጀክቱን በክልሉ በመንግስት እየተገነቡ ከሚገኙ ሌሎች ፕሮጀክቶች የተለየ ያደርገዋል ነው ያሉት፡፡
የፓርኩ ግንባታ ሲጠናቀቅም ለአካባቢው ማህበረሰብ የስራ እድል ከመፍጠር ባሻገር ለክልሉ የቱሪዝም እድገት ትልቅ አስተዋጽኦ የሚያበረክት መሆኑንም አቶ ተወለዳ ገልፀዋል፡፡