02/12/2021
የአውሮጳ ሕብረት አዲስ አበባ ከሚገኙ ልዑካኑ ብዙም የማያስፈልጉ ያላቸው ሠራተኞቹ እንዲወጡ ትዕዛዝ አስተላለፈ። የሕብረቱ ቃል አቀባይ ናቢላ ማስራሊ ዛሬ ከብራስልስ ባስተላለፉት መልእክት ከአባል ሃገራት በተሰጠው መመሪያ መሠረት እና ከዚህም ጋር በመተባበር ብዙም የማያስፈልጉ ያሏቸው ባልደረቦች እና ከእነሱ ጋር የሚኖሩ ሀገሪቱን ለቀቅቀው እንዲወጡ እንጠይቃለን ማለታቸውን አዣንስ ፍራንስ ፕረስ ዘግቧል። አክለውም ቃል አቀባይዋ ለአውሮጳ ሕብረት እና የሀገሪቱ ዜጎች ለሆኑ ሠራተኞች ደግሞ የጸጥታ ርምጃዎችን አጠናክረናል ማለታቸውም ተጠቅሷል። በርካታ የአውሮጳ ሃገራት ዜጎቻቸው ከኢትዮጵያ እንዲወጡ የጠየቁ ሲሆን የሕብረቱ ቃል አቀባይ ዜጎቹ የየመንግሥታቸውን ምክር እንዲያስተውሉም አሳስበዋል። በአንጻሩ የኢትዮጵያ መንግሥት የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ዛሬ በሰጠው መግለጫ በሀገሪቱ የጸጥታ ጉዳይ ስጋት አለመሆኑን አመልክቷል። የጸጥታውን አስተማማኝነት ለማረጋገጥም በመጪው የገና በዓል 1 ሚሊየን በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን እና ትውልደ ኢትዮጵያ እንዲሁም የኢትዮጵያ ወዳጆች ወደ ሀገር ቤት እንዲገቡ ጥሪ ቀርቧል።