13/11/2022
በሰሜን ኢትዮጵያ የተፈጸሙ "የሰብዓዊ መብቶች ጥሰቶች ምርመራ እንዲጀመር እና አጥፊዎች ተጠያቂ እንዲሆኑ" አሜሪካ ጥሪ አቀረበች።
የኢትዮጵያ ተፋላሚ ኃይላት ግጭት ለማቆም፣ ለተቸገሩ ሁሉ የሰብዓዊ ዕርዳታ አቅርቦትን ለማፋጠን፣ የሰላማዊ ሰዎችን ደሕንነት ለመጠበቅ እና መሠረታዊ አገልግሎቶችን መልሶ ለማስጀመር የደረሱበትን ስምምነት ሊያከብሩ እንደሚገባ የአሜሪካ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኔድ ፕራይስ ጥሪ አቅርበዋል። ኔድ ፕራስ ትላንት ቅዳሜ ባወጡት መግለጫ ጥሪውን ያቀረቡት የሁለቱ ተፋላሚ ኃይላት የጦር አዛዦች የፕሪቶሪያውን ሥምምነት ተግባራዊ የሚያደርግ ሰነድ ከፈረሙ በኋላ ነው።
የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሀኑ ጁላ እና የትግራይ ኃይሎች አዛዥ ጄኔራል ታደሰ ወረደ ሰነዱን ከፈረሙ በኋላ የአፍሪካ ኅብረት ባወጣው መግለጫ በትግራይ እና አጎራባች ክልሎች ለተቸገሩ ሁሉ የሰብዓዊ ዕርዳታ አቅርቦት ያለ ገደብ ለማመቻቸት ከሥምምነት መደረሱን አስታውቋል። ሁለቱ የጦር አዛዦች የተፈራረሙት ሰነድ በፕሪቶሪያ በተደረሰበት ግጭት የማቆም ሥምምነት መሠረት ለግብረ ሰናይ ሠራተኞች እና ለድርጅቶች የደህንነት ዋስትና መስጠት እንዲሁም ለሰላማዊ ሰዎች ጥበቃ ማድረግን ያካተተ ነው።
የአፍሪካ ኅብረት ያወጣው መግለጫ እንደሚያሳየው የትጥቅ አፈታት፣ አበታተን እና መልሶ ማዋሃድን የተመለከቱ ጉዳዮችን በዝርዝር የሚያብራራ የጋራ ኮሚቴ ለማቋቋም ተወስኗል። የኢትዮጵያ መንግሥት "በሰላም ሥምምነቱ በተያዘው የጊዜ ገደብ ትጥቅ የሚፈታበት እና መከላከያ ወደ መቐለ የሚገባበት ዕቅድ ላይ" ከሥምምነት መደረሱን ገልጿል። የአውሮፓ ኅብረት የአፍሪካ ቀንድ ልዩ ልዑክ አኔተ ቬበር የትጥቅ አፈታትን በተመለከተ በሁለቱ ወገኖች መካከል የተደረሰው ሥምምነት "ወደ ፊት የሚወስድ አስፈላጊ እርምጃ" እንደሆነ ገልጸዋል።