ንዋየ ወርቅ-Newaye werqe

ንዋየ ወርቅ-Newaye werqe This page is created for preaching in the order of Ethiopian Orthodox tewahedo church.

የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገት | Ascension of Lordበኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ለስም አጠራሩ ክብር ምሳጋና ይግባውና በጌታችን በአምላካችን በኢ...
13/06/2024

የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ዕርገት | Ascension of Lord

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ለስም አጠራሩ ክብር ምሳጋና ይግባውና በጌታችን በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ከሚከሩ ዘጣኝ ዐበይት በዓላት መካከል የሆነው አንዱ የጌታችን ዕርገት በዓል ነው።

ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በላ ከማረጉ በፊት 40 ቀን እንደቆየ ቅዱሳት መጻህፍት ይናገራሉ፡፡ " ደግሞ አርባ ቀን እየታያቸው ስለ እግዚአብሔርም መንግሥት ነገር እየነገራቸው፥ በብዙ ማስረጃ ከሕማማቱ በኋላ ሕያው ሆኖ ለእነርሱ ራሱን አሳያቸው።" (የሐዋርያት ሥራ 1:3) በዚህ ቃል ላይ ብዙ ነገር ተመዝግቦ እናገኛለን፡፡ 40 ቀን መቆየቱ ምክንያቶቹና ምሥጢሩ ብዙ ነው፡፡ ከነዚህም መካከል ፡-

1. የአዳም ልጅነት ስጦታ እንደተመለሰ ለማጠየቅ ፦ አዳም አባታችን በተፈጠረ በ40 ቀን ወደ ገነት በይባቤ መላእክት ገብቷል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም ዳዊት እዳለው " ወደ ላይ ዓረግህ፥ ምርኮን ማረክህ፥ ስጦታንም ለሰዎች ሰጠህ" (መዝሙረ ዳዊት 68:18) እንዳለ በምክረ ከይሲ ወድቆ የዲያብሎስ ምሮከኛ የነበረው አዳም ስጦታው (ልጅነቱ) መመለሱን ሲያረጋግጥ በ 40ኛው ቀን አርጓል፡፡

2. ዕርገቱና ትንሳኤውን እርግጥ እንደሆነ ለመናፍቃን ሊያስረግጥ ሲል፦ ክርስቶስም ይህ እንዳይሆን በሐዋ 1:2 ላይ እንደምናገኘው "በብዙ ማስረጃ ...ራሱን አሳያቸው" እንዳለ ለተጠራጣሪዎች (ዮሐ 20:24-29) ሕማሙ ሞቱ ትንሳኤው እርግጥ ፤ እውነት እነደሆነ ለማስረገጥ 40 ቀን ቆይቷል፡፡

3. የሐዋርያትን ሃይማኖት ለማጽናት፦ ተስዕሎተ መልክ (የሰው ልጅ ተፀንሶ በማህፀን ሳለ ሙሉ የሰው ቅርጽ እስከሚይዝ ድረስ ያለው ጊዜ) በ40 ቀን እንየሚፈጸም ክርስቶስም በጽንስ ያለውን የሐዋርያትን እምነት ለማጽናት ሲል 40ቀን ቆይቷል፡፡ "ደግሞ አርባ ቀን እየታያቸው ስለ እግዚአብሔርም መንግሥት ነገር እየነገራቸው፥" (የሐዋርያት ሥራ 1:3) ክርስቶስ በ 40 ቀን ቆይታው ብዙ ትምህሮቶችን አስተምሯቸዋል፡፡ ስለ እግዚአብሔርም መንግሥት በተለይም መጽሐፈ ኪዳንን አስተምሯል፡፡


ክርስቶስ ያረገው በደብረዘይት ጥግ በምትገኘው በቢታንያ ነው፡፡ ሉቃ 24:50 ቢታንያ ከኢየሩሳሌም 15 ምዕራፍ ትርቃለች፡፡ ቢታንያ አልአዛርን ከሞት ያስነሳበት ፤ መግደላዊት ማርያም ሽቱ በእግሩ አፍሰሳ ንስሐዋን የተቀበለበት እንዲሁም ወደ ኢየሩሳሌም ሲሄድ ሆነ ሲመጣ ያርፍባት የነበረች ከተማ ናት፡፡ እርሷም ምትገኘው ከኢየሩሳሌም በስተ ምስራቅ ነው፡፡ በዚህ እደሚያርግ ነብዪ ዳዊት እንዲህ ብሎ ተንብዮ ነበር፡፡ " በምሥራቅ በኩል ወደ ሰማየ ሰማያት ለወጣ ለእግዚአብሔር ዘምሩ፤ የኃይል ቃል የሆነ ቃሉን፥ እነሆ፥ ይሰጣል።" (መዝሙረ ዳዊት 68:33)


ሊቃውንተ ቤ/ን የጌታችንን ዕርገት ወቅቱን ከልደቱ ጋር አገናኝተው ደስ በሚያሰኝ ሚስጢር ይተረጉሙታለ፡፡ በተለይ ስለ ጠፈር ምርምር ትልቅ ዕውቀት እንዳለው የሚነገርለት አባታችን ቅዱስ ያዕቆብ ዘስሩግ እንዲህ በማለት ያብራራል "ጌተችን የተወለደው በወርኃ ታኅሳስ ነው በዚህ ወቅትም ፀሐይ ከምህዋራ ዝቅ የምትልበት ጊዜ ነው፡፡ እውነተኛው ፀሐይ ክርስቶስም በፍጹም ፍቅሩ ዝቅ ብሎ በዚህች ወር ተወለደ፡፡ እንዲሁም በወርኃ ግንቦቶ ፀሐይ ከምህዋሯ ከፍ የምትልበት ከሌላው ጊዜ በበለጠ የምታሸበርቅበት የምታበራበት ወቅት ነው፡፡ እውነተኛው ፀሐይ ክርስቶስም ከምድር ከፍ ብሎ በርቀት ሳይሆን በርህቀት ዐረገ፡፡"

ከበዓሉ ረድኤት በረከት ያሳትፈን ....
አሜን!!

Natnael Yaboneh

እንደዚህ እንደሆነ አላሰብኩም ነበር!በነገራችን ላይ ትዕግስትህን ሳላደንቅ አላልፍም የምር ! እኔ እኮ ትዕግስት ነው ያጣሁት ብታይ መጠበቅ ታከተኝ ነው የምልህ !! ደሞ እኮ ስላንተ ብዙ ጊዜ...
31/03/2024

እንደዚህ እንደሆነ አላሰብኩም ነበር!

በነገራችን ላይ ትዕግስትህን ሳላደንቅ አላልፍም የምር ! እኔ እኮ ትዕግስት ነው ያጣሁት ብታይ መጠበቅ ታከተኝ ነው የምልህ !! ደሞ እኮ ስላንተ ብዙ ጊዜ ነው የምሰማው ግን አላደመጥኩም መሰለኝ መልሼ ረሳለሁ። በሰላሳ ዓመት እኮ አንድ ልጅ ተወልዶ ለጎልማሳነት ይበቃል። ቆይ ጠብቄስ ባይሆን የሚል የእምነት መጉደል ውስጤን እያስፈራው አልቻልኩም ነው ምልህ።

ደግሞ መጨረሻ ላይ ያገኘኸውን ስሰማ እውነት ቀናውብህ ! ግን እንዴት ይህ ሁሉ ዓመት እዛ በስቃይ ተኝተህ "ልትድን ትወዳለህ" ማለት ምን ማለት ነው ? ያው ችኩል አይደልሁ ምን ማለት እንደሆነ መጠየቅ ሲገባኝ ለፍርድ ቸኮልኩ ፣ ግን ደግሞ ህሊናዬ ሲወተውተኝ አንድ ሊቅ ጋር ሄጄ ጠየኳቸው ባይገርምህ እኚህ ሊቅ ሳይናገሩ የሚያስፈሩ ግርማ ሞገሳቸው ከገጻቸው የሚነበብ ሰው ናቸው። በጣም ከኛ ርቀው ሄደዋል ከኔ አንፃር ሳያቸው እሳቸው እዚህ አይደሉም ልባቸው ሌላ ሰማይ ላይ ነው። ተመልከት ደግሞ ድፍረቴ ከኔ ጋር ሳነጻጽራቸው ወይ ጉድ ! ሌላ ጊዜ ስለእሳቸው በሰፊው አጫውትሃለው። ብቻ እንዲህ ግራ ሲገባኝ ሄጄ ማናግራቸው እሳቸው ነው። ያው እንደለመድኩት ፈራ ተባ እያልኩ ጠየኳቸው። አንተ ለካ የጠየቀህ ለምክንያት ነው ምን እንዳሉኝ ታውቃለህ ? በመጀመሪያ እርሱ ሁሉን ያውቃል ! እሱን ብቻ ሳይሆን የተሰወረውን በልብ ያለውን ሁሉ ያውቃል ! ለዚህ ነው ለብዙ ጊዜ እንዲህ እንደነበር አውቆ ብሎ የሚጀምረው ሲሉኝ ገና ሳይጨርሱ ከአፋቸው ላይ መንተፍ አደረኩና ታድያ እሱ አይደል እኔ የገረመኝ ስላቸው ፈገግ አሉና የጠየቀው ለምን መሰለህ ብለው ማብራራታቸውን ቀጠሉ ፦
+ አንደኛ ፍጹም ሰው መሆኑን ለማጠቅ ማለት ሁሉን ነገር ማወቅ የማይችል የነበረ ሥጋን መዋሃዱን ለመንገር ነው አሉኝ ! ባይገርምህ አንድም አንድም እያሉ ነው የሚያስረዱኝ እና በጣም ነው የምወድላቸው የምር !
+ ቀጠሉና አንድም ለድኅነቱ ኃላፊነት እንዲወስድ ሲሉኝ እንዴ አባ ሊድን ፈልጎ አደል እንዴ ይህ ሁሉ ጊዜ እዚያ የተቀመጠው አልኳቸው ። ቀጠሉና አየህ ልጄ ሲፈጠርን ግዕዛን ያለው አድርጎ ነው። ማለት አባ ገዕዛን ሲሉ ? አልኳቸው ። እሳቸውም ግዕዛን ቃሉ የግእዝ ነው ነፃ ፣ ነፃነት እንደማለት ነው አግአዚ ሲባል አልሰማህም ? አዎ አባ ስላቸው ነፃ አውጪ ማለት አንተ ከምታስታውሰው ደግሞ የሰኞ ውዳሴ ማርያም ላይ በመጀመሪያው ክፍል "አዳምን ነፃ ያወጣውና .." ይላል ይህን በግእዙ የሚለው "አግአዞ ለአደም" ነው። እና ነፃ ፈቃድ ያለው ፍጡር አድርጎ ነው የፈጠረን ታድያ ይህ ነፃነታችንን በምንም አይነት መንገድ ሊወስድን አይፈልግም ለዚህ ነው ሊፈውስ ሲል እንኳን ልትድን ትወዳለህን ብሎ የሚጠይቅ ። እኔም መረዳቴን ለመግለጽ ጭንቅላቴን በመነቅነቅ ገለጥኩላቸው።

በጣም የገረመኝ የዳንከው ያ ሁሉ ዓመት ይፈውሰኛል ብለህ ባሰብከው ውሃ አለመሆኑ ነው። በነገራችን ላይ ይህንንም ጠይቄያቸዋለሁ በደንብ ነው አስፍተው የነገሩኝ ምን አሉኝ መሰለህ
እሱንማ ካነሳህ ነገርን ከስሩ ነው ብለው ጀመሩ ። በሰው ልጅ በደል ምክንያት በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ትልቅ ክፍተት ተፈጥሮ ነበር ። ግን እግዚአብሔር አባት ነውና ረድኤቱን ከሰው ልጆች አላራቀም ስለዚህም በዚያ የምህረት ቤት በምትባለው ቤተ ሳይዳ ብዙ ህሙማን ነበሩ የእግዚአብሔርም መልአክ ውሃውን ባናወጠው ጊዜ ቀድሞ ከውሃው የገባ ካለበት በሽታ ይድናል። እንዴ አባ ለምን የቀደመ ብቻ አልኳቸው እሳቸውም ቅድም ያልኩህ ነው በሰውና በእግዚአብሔር መካከል ትልቅ የጥል ግድግዳ ነበር ቢሆንም እግዚአብሔር በድላችኁኛል ብሎ አላጠፋቸውም ይልቁንም ምንም ብትበድሉኝ እኔ ከናተጋር ነኝ ሲል በረድኤት ይገለጥ ነበር። አሁንም እንድምናየው ማለት ነው። እርሱ ቸር ስለሆነ ነው ለኃጥኡም ለጻድቁም እኩል ዝናብ የሚያዘንበው እኩል ፀሐይ የሚያወጣው። ልክ አባት ልጄ አጠፋ ብሎ እህል ውሃ እንደማይከለክል ማለት ነው እርሱ ደግሞ ከዚያ በላይ ነው። ታድያ ተነሳና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ ማለቱ ቀድሞ ፍጹም ሰው መሆኑን "ልትድን ትወዳለህ" ብሎ እንዳጠየቀ ሁሉ አሁን ደግሞ መለኮት የተዋሀደው ሥጋ ፍጹም አምላክ መሆኑን ለማጠየቅ በቃሉ ብቻ "ተነስና አልጋህን ተሸክመ ሂድ" አለው። አንድም ደግሞ ይህ ሰው ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና ጌታችን በውሃ ቢፈውሰው ከእርሱ አዳኝነት ይልቅ ለዚህ ሁሉ ዓመት መጠበቁ ድኅነት እንዳስገኘለት ያስባልና ነው።

ደስ ሲሉ በናትህ እንዴት አድርገው እንዳስረዱኝ ! አንተ ግን የምር በውሃ ብትፈወስ እንደዚያ ታስብ ነበር ? ለነገሩ ተወው እንኳን አንተ እኔ እራሱ ትንሽ ስራ ሰርቼ የእርሱ ጥበቃ ፣ ረድኤት እንዳገዘኝ ማሰብ እንኳ አልችልም በጣም ያሳዝናል። ብታይ በዚህ ዘመን እኔነት ነግሷል። እኔ እኔ እኔ ፈጣሪን ረስተናል ማሰብ ተስኖናል አንዳንዶቻን እንደውም በሕወታችን ፈጽሞ እግዚአብሔር እንዲገባ አንፈልግም ግን አይገርም እርሱ የፈጠረን የእርሱ ስራዎች ሆነን። እርሱ የፈጠረውን አየር እየማግን በረድኤቱ ጥላ ስር እየተከለልን አንፈልግህም በኛ ህይወት አያገባህም ስንለው። ብቻ ማስተዋሉን ያድለን!! አልጨረስኩልህም !!!

ናትናኤል ያቦነህ
አዲስ አበባ, ኢትዮጵያ

ኒቆዲሞስኒቆዲሞስ ከፈሪሳውያን ወገን የሆን የአይሁድ መምህራቸው (ምሁረ ኦሪት)የነበረ ሊቅ ነው።   ኒቆዲሞስ መምህር ብቻ ሳይሆን የአይሁድ ሹም እንዲሁም ባለጸጋ ነበር። በዮሐ 3፡1 ጀምረን ...
02/04/2023

ኒቆዲሞስ
ኒቆዲሞስ ከፈሪሳውያን ወገን የሆን የአይሁድ መምህራቸው (ምሁረ ኦሪት)የነበረ ሊቅ ነው። ኒቆዲሞስ መምህር ብቻ ሳይሆን የአይሁድ ሹም እንዲሁም ባለጸጋ ነበር። በዮሐ 3፡1 ጀምረን እንደምናነበው ይህ ኒቆዲሞስ የተባለው መምህር ማታ ማታ ከጌታ ዘንድ እየሄደ ይማር ነበር። ሊቃውንተ ለምን ማታ ማት እየሄደ ይማር እንደነበር ሲተረጉሙት፦ አንድም ከማመኑ አስቀድሞ ፤ ለምን ቢሉ አሁን ድረስ ክርስቶስ አልመጣም ገና ይመጣል ብለው ከሚያምኑ ከአይሁድ ወገን ስለሆነ ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ መሲህ ነው ብሎ አምኖ አልተቀበለም ነበርና በማታ አለ (ወደ ብርሃን አልተሻገረምና)።
አንድም ደግሞ መማር ቢፈልግም መምህር ነበርና አይሁድ ከጌታ እግር ስር ቁጭ ብሎ ሲማር ቢያዩት “መምህር ነኝ እያለ እስከ ዛሬ ድረስ ሳይማር ኖሯል እንዴ ?” እንድይሉት ውዳሴ ከንቱን ሽቶ በቀን ሳይሆን በምሽት እየሄደ ይማር ነበር። አንድም ደግሞ የቀን ልቦና ባክና (በሐሳብ የሚባክን)ነው ፤ የሌሊት ልቦነ ግን ክት ነው ፤ ብሎ በምሽት እየሄደ ይማር ነበር።
አንድም ደግሞ አይሁድ“እመቦ ዘአምነ ቦቱ ከመ ክርስቶስ ይሰደድ እምኩራብ” በክርስቶስ የሚያምንና ትምህርቱን የሚሰማ ቢገኝ ከማህበራችን ይለይ ብለው ሕግ አውጥተው ነበርና የአይሁድን ዛቻና ማስጠንቀቂያ ፈርቶ በማታ እየሄደ ይማር ነበር።(ዮሐ 9፡22) “ከዚህም ጋር ከአለቆች ደግሞ ብዙዎች በእርሱ አመኑ ነገር ግን ከምኩራብ እንዳያስወጧቸው በፈሪሳውያን ምክንያት አልመሰከሩለትም ከእግዚአብሔር ክብር ይልቅ የሰውን ክብር ወደዋልና።” (ዮሐ 12፡42) እንደተባለ ኒቆዲሞስም ወደ ጌታ መጥቶ መማሩ እንዲታወቅ ያልፈለገው ለዚህ ነበር።
ኒቆዲሞስ ጌታችን ራሱ ለብቻቸው በቃል ምልልስ እያናገረ ጥያቄያቸውን እየመለሰ ካስተማራቸው ጥቂት ዕድለኛ ሰዎች አንዱ ነው። ወደ ጌታም በመጣ ጊዜ እንዲህ ነበር ያለው “መምህር ሆይ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔር እንደመጣህ እናውቃለን ” (ዮሐ 3፡3) ምልክት ያለው ተአምሩን ሲሆን ያን ጊዜ ጌታችን በፋሲካ በዓል ተአምር ያደረገበት ወቅት ነበር። በዚህ ምልክትም በጌታችን ካመኑት መካከል ኒቆዲሞስ አንዱ ነበር።
ኒቆዲሞስ ስለ ጌታችን “እግዚአብሔር ካንተ ጋር ነው” ብሎ ቢመሰክርም ወጣኒ(ጀማሪ) ክርስቲያን ነበርና ሊከተለው ግን አልፈለገም።
ዛሬም ብዙዎቻችን በተግባር ያልተገለጠ በልብ ብቻ ያለ ክርስትና ነው ያለን ፤ ስለ እምነታችን ሲነሳ ደስ የማይለን ፤ በአለባበሳችን ፣ በአመጋገባችን ፣ በንግግሮቻችን ፣ በትምህርት ቤት ፣ በሥራ ቦታችን እምነታችን የማይገለጥ የስም ክርስትና የያዝን ከኒቆዲሞስ የባስን ብዙ አለን። ነግር ግን ስለ ክርስትናችን መከራ ልንቀብል እንጂ ልናምን ብቻ አይደልምና በተግባር የተገለጠ ክርስትና እንደሚያስፈልገን መጽሐፍ ይናገራል። (ፊሊ 1፡29)
የኒቆዲሞስ ክርስትና በልቡ ብቻ የቀረ አልነበረም ፤ አድጎ ለመፈትን በቅቷል። የካህናት አለቆች ክርስቶስን ሊይዙት ይፈልጉ ነብርና ሎሌዎቻቸውን ልከው ይዘውት እንዲመጡ ቢልኳቸው ከጣዕመ ትምህርቱ የተነሳ ባዶ እጃቸውን ተመልሰዋል። በዚህም ጊዜ ለምን ይዘውት እንዳልመጡ ሲጠይቋቸው “እነደዚህ ዓይነት ትምህርት ከቶ ሰምተን አናውቅም” ብለው መለሱ ፤ የካህናት አለቆችም ተቆጧቸው ፤ ኒቅዲሞስ እዚያው ነበርና ደፍሮ ስለ ክርስቶስ በግልጥ መመስከር ባይችልም “እርሱን ሳንሰማ መፍረድ ተገቢ ነውን ?” ብሎ ከክርስቶስ ዘንድ መማር ምን እንደሆነያውቃልና መጀመሪያ በክርስቶስ ፊት የመሰከረውን እምነቱን አሁን ደግሞ አድጎ በፈሪሳውያን የካህናት አለቆች ፊት በፈሊጥ መስክሯል።
ከዚህ ከፍ ሲል ደግሞ አምላካችን ለሰው ልጅ ሁሉ ቤዛ ሆኖ ተሰቅሎ ሲሞት ከቅዱስ ዮሐንስ በቀር ከዋለበት የዋሉ ካደረብት ያደሩ ፈርተው ሲሸሹ የማታ ተማሪ የነበረው ፣ ከምኩራብ ያባርሩኛል ብሎ ሲፈራ የነበረው ኒቆዲሞስ ክርስትናው አብባና አፍርታ አይሁድ ገርፈው በመከራ አሰቃይተው የገደሉትን ክርስቶስ በማታ ሳይሆን በቀን በብርሃን (ሳይደበቅ በግልጥ) ከአርማትያው የሴፍ ጋር በመሆን ክቡር ሥጋውን ገንዘው ቀብረውታል።
ቤተክርስታያናችንም ይሄን “ኒቅዲሞስ”ተብሎ የተሰየመውን የዐቢይ ጾም ሳምንት ከኒቆዲሞስ ሕይወት እንድንማር በማዘከር ነው። እኛም ልክ እንደ ኒቆዲሞስ ሥልጣናችን ፣ ክብራችን፣ ማዕረጋችን ፣ ሐብታችን ሳይገታን ዛሬም ክርስቶስ ከሚሰበክባት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቅጥር ውስጥ ተገኝተን ተምረን በተግባር የተገለጠ እና በፈተና አልፎ በየጊዜው የሚያድግ ክርስትና ሊኖረን ያስፈልጋል።
ልክ እንደ ኒቆዲሞስ በትንሽ ተጀምሮ ፍጻሜው የሚያምር ክርስትና እንዲኖረን አምላካችን አምላከ ቅዱሳን ይርዳን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር።
ንዋየ ወርቅ-Newaye werqe

እንኳን ለዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት በሰላም አደረሳችሁ!ገብርኄርሊቁ ቅዱስ ያሬድ የዐቢይ ጾም ሳምንታትን በሰየመው መሠረት ስድስተኛው ሳምንት “ገብርኄር” በመባል ይታወቃል። ገብርኄር ማለት ...
26/03/2023

እንኳን ለዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት በሰላም አደረሳችሁ!
ገብርኄር

ሊቁ ቅዱስ ያሬድ የዐቢይ ጾም ሳምንታትን በሰየመው መሠረት ስድስተኛው ሳምንት “ገብርኄር” በመባል ይታወቃል። ገብርኄር ማለት “ቸር አገልጋይ” ማለት ሲሆን ሊቁ በመዝሙሩ ስለ ቸር አገልጋይ እንዲህ ሲል ዘምሯል ፦

“መኑ ወእቱ ገብርኄር ወምዕመን ዘይረክቦ እግዚኡ
በምግባረ ሠናይ ወይሠይሞ ዲበ ኩሉ ንዋዩ...
ጌታው በበጎ ሥራ የሚያገኘውና ባለው ሁሉ ገንዘብ
ላይ የሚሾመው ቸርና ታማኝ አገልጋይ ማነው?
ዳግመኛ እግዚአብሔር እንዲህ አለው። በጥቂቱ
የታመንህ አንተ በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ
ግባ።

ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም ስለቸር አገልጋይነትና ታማኝነት በዚህ ሳምንት በሰፊው ታስተምራለች። በተለይ በማቴ 25፡14(ሉቃ 19፣11፦27) ላይ ጌታችን ሰለ መንግስተ ሰማይት እንዲሁም ስለ ቸርነትና ታማኝነት በምሳሌ መስሎ ያስተማረውን ታሪክ በመጥቀስ እኛ ልጆቿ ታማኝና ቸር እንድንሆን ትሰብካለች። ቅዱስ ያሬድም ከላይ ያየነውን ድርሰት የደረሰው በዚህ ታሪክ ላይ መሠረት በማድረግ ነው። ታሪኩ እንዲህ ነው።

“ወደ ሌላ አገር የሚሄድ ሰው ባሮቹን ጠርቶ ያለውን ገንዘብ እንደ ሰጣቸው እንዲሁ ይሆናልና፤ ለእያንዳንዱ እንደ ዓቅሙ፥ ለአንዱ አምስት መክሊት ለአንዱ ሁለት ለአንዱም አንድ ሰጠና ወደ ሌላ አገር ወዲያው ሄደ። አምስት መክሊትም የተቀበለው ሄዶ ነገደበት ሌላም አምስት አተረፈ፤ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ። አንድ የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቈፈረና የጌታውን ገንዘብ ቀበረ። ከብዙ ዘመንም በኋላ የእነዚያ ባሮች ጌታ መጣና ተቆጣጠራቸው።

አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና ሌላ አምስት መክሊት አስረክቦ። ጌታ ሆይ፥ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ፥ ሌላ አምስት መክሊት አተረፍሁበት አለ። ጌታውም መልካም፥ አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው።

ሁለት መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ ጌታ ሆይ፥ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፤ እነሆ፥ ሌላ ሁለት መክሊት አተረፍሁበት አለ። ጌታውም መልካም፥ አንተ በጎ፥ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፥ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው።

አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ። ጌታ ሆይ፥ ካልዘራህባት የምታጭድ ካልበተንህባትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ ፈራሁም ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት፤ እነሆ፥ መክሊትህ አለህ አለ። ጌታውም መልሶ እንዲህ አለው።

አንተ ክፉና ሃኬተኛ ባሪያ፥ ካልዘራሁባት እንዳማጭድ ካልበተንሁባትም እንድሰበስብ ታውቃለህን ስለዚህ ገንዘቤን ለለዋጮች አደራ ልትሰጠው በተገባህ ነበር፥ እኔም መጥቼ ያለኝን ከትርፉ ጋር እወስደው ነበር። ስለዚህ መክሊቱን ውሰዱበት አሥር መክሊትም ላለው ስጡት፤ ላለው ሁሉ ይሰጠዋልና ይበዛለትማል፤ ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል። የማይጠቅመውንም ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት፤ በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል።”

በዚህ ምሳሌያዊ ትምህርት ባለጸጋ የተባለው የመክሊቱ አዳይ ልዑል እግዚአብሔር ነው፤ አጋልጋዮች የተባሉት ደግሞ ምዕመናን ናቸው። መክሊት የተባለው ደግሞ ለምዕመናን የተሰጣቸው ጸጋዎች ናቸው። አትርፈው የመጡት በተሰጣቸው ጸጋ ለራሳቸው ተጠቅመው ለሌላውም ተርፈው መልካም አርአያና ምሳሌ ሆነው የሚኖሩ ሲሆኑ የተሰጠውን መክሊት ቀብሮ ያንኑ መልሶ የሰጠው ደግሞ ጸጋና እድሜ በከንቱና በዋዛ ነገር ሲያባክን የኖረ ምእመን ምሳሌ ናቸው።

በመጨረሻም አትርፈው የመጡት የተሸለሙት መካነ ዕረፍት መንግስተ ሰማያትን ሲሆን ቀብሮ የመጣው የተፈረደበት ደግሞ ትሉ ወደ የማያንቀላፋበት እሳቱ የማይጠፋበት ገሃነመ እሳት ነው።

ባለ 5 እና ባለ ሁለት የተባለው ፍጹም ትምህርት ተምሮ መክሮ አስተምሮ ራሱን አስመስሎ ያወጣ ነው። ቅዱስ ጴጥሮስ ቀለሜንጦስን ጳውሎስ ጢሞቲዎስን እንዳወጡ ፤ ባለ አንድ የተባለ ደግሞ ተምሮ እሳት ስለት አሳይተው ቢያስክዱኝ ፤ መናፍቃን ተከራክረው ምላሽ ብያሳጡኝ ብሎ ፈርቶ ሃይማኖቱን በልቡ የያዘ(ሳያስተምር የቀረ) ምሳሌ ነው።
ይህን ባለ አንዱን ጌታው እንዲህ ይለዋል ፤ ወጥተህ ወርደህ ካላስተማርክ ሹመትህን ብታስረክበኝ በተገባ ፤ ወጥቶ ወርዶ ለሚያሰተምር በሰጠሁት ነበር። አንድም ደግሞ ከሁለት ከሶስት ጆሮ ባደረስከው እኔ ተራድቼ ባስፋፋሁት ነበር። በመጨረሻም ጌታ እንዲህ ይላል የሱን ሹመት አንሱና ላተረፈው ደርቡለት እርሱን ግን አውጡት። ነገር ግን ከመንግስተ ሰማይ አይወጣም በመምህነት መግባት ቢቀርበት በሕዝባዊነት(በምዕመንነት) ይገባልና።

አንድም ባለ አምስት ሙሴ ነው ፤ አምስት መጻሕፍት አሉትና። ባለ ሁለት ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት መልዕክታትን ጽፋልና አንድም የብሉያን የሐዲስ ኪዳንን በአንደነት አስተምሯልና። ባለ አንድ የተባለው ወስዶ የቀበረው ደግሞ ይሁዳ ነው።

አንድም ባለ አምስት ሊቀ ጳጳሳት ይህም ሲመተ ጳጳሳት ፣ ሲመተ ቀሳውስት፣ ሲመተ ዲያቆን ፤ ማጥመቅ ፣ ማቁረብ
ናቸው። ባለሁለት ቄስ ማጥመቅ ና ማቁረብ ባለ አንድ ዲያቆን ይህም ተልእኮ ነው።

አንድም ባለ አምስት እምነት ፣ ፍሥሐ(ደስታ)፣ ምሕረት ፣ ትእግስት እና ተስፋ ናቸው። ባለ ሁለት እምነትና ፍሥሐ ፤ ባለ አንድ እምነት ናቸው።

አንድም ባለ አምስት ጥምቀት ፣ ተአምኖ ኃጢአት(ኃጢአትን ማመን)፤ ከዊነ ሰማዕት(ሰማዕት መሆን) እና ተባሕትዎ ምንኩስና ናቸው። ባለሁለት ጥምቀት እና ተአምኖ ኃጢአት ፣ ባለ አንድ ጥምቀት ናቸው።

አንድም ባለ አምስት ፍጹም ባለ ጸጋ ፤ ባለ ሁለት እንድ መጠኑ ባለ ጸጋ ፤ባለ አንድ ፍጹም ድኃ ናቸው።

ከላይ እንደተገለጸው ሊቃውንተ ቤተ ክርስትያን በምሳሌ የተገለጸውን መክሊት አብራርተው ተርጉመውታል። (ትርጓሜ ወንጌል ዘማቴዎስ)የእያንዳንዳችን ጸጋ ይለይ እንጂ የሁሉም ጸጋ ሰጪ ቅዱስ እግዚአብሔር ነው። ዋናው ቁም ነገር በተሰጠው ጸጋ አትርፎ መገኘት እንጂ የጸጋው ብዛትና ማነስ አይደለም። ይህን ደግሞ የምንረዳው ምንም እንኳን ባለ አምስትና ባለ ሁለት መክሊት የተቀበሉት ባሪያዎች መክሊታቸው ቢበላለጥም ሁለቱም እኩል በመመስገናቸው ነው ፤ ይህም ብዙ መቀበላቸው ሳይሆን ፤ አትርፈው በመገኘታቸው ነበር።

ከዚህ ወንጌል ክፍል የምንረዳው የመጀመሪያ ነጥብ ጸጋ ከእግዚአብሔር እንድሚስጥ ፤ እግዚአብሔር አምላካችን ለሁላችንም ይብዛም ይነስ ጸጋውን እንደሰጠን ነው። ሌላው ደግሞ በዚህ በተሰጠን ጸጋ አትርፈን ካልተገኘን እንደሚያስጠይቅና ለፍርድ እንደሚያበቃ ነው።

በወንጌሉ ላይ አትርፎ መገኘት ምን ዓይነት ሽልማት እንደሚያሰጥ ተመልክተናል። ስንቶቻችን ነን የተሰጠንን መክሊት የቀበርን? ከራሳችን አልፈን ለብዙዎች መትረፍ ስንችል በስንፍና ገመድ ታስረን እንደ ባለ አንዱ ባሪያ ምክንያት እየደረድርን ከመንገድ የወጣን? ወዳጄ እግዚአብሔር ቸር ነው ፤ በተሰጠህ መክሊት ከታመንክ በብዙ ይሾምሃል።

ይህን ሳምንት ስንጾም ጸጋዬ ምንድነው? ምንስ አተረፍኩበት በማለት ሊሆን ይገባል። ለፍርድ ከመጠራታችን በፊት በተሰጠን ጸጋ አትርፈን በፍርድ ሰዓት “አንተ በጎ፥ ታማኝም ባሪያ፤ በጥቂቱ ታምነሃል፥ በብዙ እሾምሃለሁ፥ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” የሚለውን ቃል እንድንሰማ የአምላካችን ቅዱስ ፈቃድ ይሁንልን።

††††††
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር።
ንዋየ ወርቅ-Newaye werqe

ደብረ ዘይትየዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት ደብረ ዘይት በመባል ይታወቃል።  ደብር ማለት ተራራ ማለት ሲሆን በአንድ ላይ የዘይት ተራራ (Mount of Olives)የሚል ትርጉም ይሰጠናል።  ይህ...
19/03/2023

ደብረ ዘይት

የዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት ደብረ ዘይት በመባል ይታወቃል። ደብር ማለት ተራራ ማለት ሲሆን በአንድ ላይ የዘይት ተራራ (Mount of Olives)የሚል ትርጉም ይሰጠናል። ይህ ተራራ የሚገኝው በኢየሩሳሌም ከተማ ውስጥ ሲሆን ስያሜውንም ያገኘው በተራራው ላይ ብዙ የወይራ ዛፍ ስላለበት ነው።

አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህች ተራራ ላይ ዳግም ስለ መምጣቱ(ዳግም ምጽአቱ)አስተምሯል።
(ማቴ 24፤1 ጀምሮ) ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም በተለይ በዚህ ሳምንት ስለ ክርስቶስ ዳግም ለፍርድ መምጣት የምታስብበት ጊዜ ስለሆነና ጌታችንም ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ተራራ ላይ ዳግም ስለ መምጣቱ ስላስተማረ ይህ ሳምንት በተራራው ስም ደብረ ዘይት ተብሎ ተሰይሟል።

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝ 49፤2 ላይ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተወልዶ ፤ ተሰቅሎ ፤ ሞቶ የሰውን ልጅ ከባርነት ነፃ ካወጣ በኋላ ዐርጎ እንደማይቀር ዳግም እንደሚመጣ በትንቢት መነፅር በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ሲናገር “እግዚአብሔርሰ ገሃደ ይመጸእ ወአምላክነሂ ኢያረምም ፦ እግዚአብሔር ግልጥ ሆኖ ይመጣል ዝምም አይልም” በማለት ክርስቶስ ከመወለዱ አስቀድሞ ዘምሯል።

ግልጥ ሆኖ ይመጣል ሲል እንደ ቀደመው ሳይሆን በግርማ መለኮት ፤ በክበበ ትስብእት ፤ በኃይል ይመጣል ሲል ነው። ዝምም አይልም ማለቱ ጌታችን ለሰው ልጅ ድኀነት ሲል መከራና ስቃይ ሲያበዙበት ታግሶ ዝም እንዳለው ሳይሆን ኃጢአተኛውን ገሃነምን ጻድቁን ደግሞ መንግስተ ሰማያትን ሊያወርስ ለፍርድ እንደሚመጣ ሲናገር ነው።

በማቴ 24፤3 ጀምሮ እንደምናነበው ጌታችን ለሐዋርያቱ ስለ ዳግም ምጽአቱ መድረስ ምልክቶች ምን እንደሆኑና እንዴት እንደሚሆን እንጂ እርግጠኛ ቀኑ መች እንደሆነ አልነገራቸውም። ይህንንም ከባሕርይ አባቱ ከአብ ፤ እንዲሁም ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ በቀር መላዕክት እንኳን እንደማያውቁት ነግሯቸዋል። (ማቴ 24፤36) ለዚህም ነው “ቀኒቱንና ሰዓቲቱን አታውቁምና እንግዲህ ንቁ” የተባለው (ማቴ 25፤13)

አምላካችን ከተናገራቸው ዳግም ምጽአቱ መቃረቡን የሚያሳዩ ምልክቶች መካከል ክርስቶስ ነኝ ባዮች መብዛትና ብዙዎችን ማሳት ፤ የጦርነት መብዛት፤ ስለ ክርስቶስ ስም መገደል መሰቃየት ፤ የሐሰተኞች ነቢያት መብዛትና የፍቅር መቀዝቀዝ ጥቂቶቹ ናቸው። ጌታችንም በመቀጠል በማስጠንቀቅ እንዲህ በማለት ተናግሯል “በዚያች ወራት ለርጉዞችና ለሚያጠቡ ወዮላቸው። ነገር ግን ሽሽታችሁ በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ”

“በዚያች ወራት ለርጉዞችና ለሚያጠቡ ወዮላቸው” ማለቱ ኃጢአትን በሐልዮ(በማሰብ)ፀንሰው በነቢብ(በመናገር) ወልደው በገቢር(በመስራት) ለሚያሳድጉ ሰዎች ወዮላቸው መከራ ነፍስ አለባቸውና። አንድም ደግሞ ምዕመናንን በትምህርት ፀንሰው በትምህርት ወልደው በትምህርት ለሚያሳድጉ መምህራን ወዮላቸው መከራ ሥጋ አለባቸውና ሲል ነው።

“ነገር ግን ሽሽታችሁ በክረምት ... እንዳይሆን ጸልዩ” ሲል ደግሞ ቡቃያና ቅጠል እንጂ ፍሬ በማይገኝበት ክረምት ስደት አስቸጋሪ እንደሆነ ሁሉ መንፈሳዊ ፍሬ ሳታፈሩ ለፍርድ እንዳልመጣ ጸልዩ እንዲሁም በክረምት ምድር እንደምትጨቀይ የናንተም ሕይወት በኃጢአት ጨቅይቶ መንገዳችሁም በክፋት ተመልቶ ሳለ እንዳልመጣ ፀልዩ ማለቱ ነው።

“በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ” ማለቱ ሌሎቹን ቀን በሥራ አሳልፈን ሰንበት ዕረፍት ናትና በሰንበት እንደምናርፍ ሁሉ በሃይማኖት ብቻ ሳላችሁ ምግባር ትሩፋት ሳትሰሩ ሞት እንዳይታዘዝባችሁ ወይም ምግባር ትሩፋት ባቆማችሁ ጊዜ ፤ በደከማችሁ ጊዜ እንዳልመጣ ጸልዪ ማለቱ ነው።(ያዕ 2፤14)

በኃጢአት ወድቀን ሳይሆን በምግባር ትሩፋት ፤ በጾም በጸሎት ጸንተን የዓለም ብልጭልጭ ሳያታልለን ለእርሱና ለእርሱ ብቻ ተገዝተን በንስሐ ታጥበን እንደ አምስቱ ልባም ቆነጃጅቶች ተዘጋጅተን ሙሽራውን እንድንጠብቀው የአምላካችን ፈቃድ ይሁንልን አሜን!

“አመ ትመጽእ ለኲንኖ ምስለ ደመ ገቦ አእጋር አማኅጸንኩ ነፍስየ ውስተ እዴከ ክቡር ኢየሱስ ክርስቶስ እግዚአ ሰማያት ወምድር”

“አቤቱ የሰማይና የምድር ፈጣሪ ኢያሱስ ክርስቶስ ሆይ በዕለተ ዓርብ ከጎንህ ከፈሰሰው ከእግሮችህ ከወረደው ደም ጋር ለፍርድ በመጣህ ጊዜ ነፍሴን በክብርት እጅህ አደራ አስጠብቃለሁ”
(ተአምረ ኢየሱስ)
††††††

ንዋየ ወርቅ-Newaye werqe

“ኢየሱስም ተነሳና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለው” ዮሐ ፭-፰መፃጉዕየዐቢይ ጾም አራተኛ ሳምንት መጻጉዕ በመባል ይታወቃል። መፃጉዕ የሚለው ቃል የግእዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙም ድውይ ፤ በአልጋ የ...
12/03/2023

“ኢየሱስም ተነሳና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ አለው” ዮሐ ፭-፰

መፃጉዕ
የዐቢይ ጾም አራተኛ ሳምንት መጻጉዕ በመባል ይታወቃል። መፃጉዕ የሚለው ቃል የግእዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙም ድውይ ፤ በአልጋ የሰለለ ፤ ለብዙ ጊዜ በበሽታ በአልቃ ቁራኝነት የቆየ ማለት ነው።
በዚህ በአራተኛው ሳምንት ለ 38 ዓመት በበሽታ ወድቆ የነበረውን መፃጉዕን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያዳነበት የሚታሰብበት ሳምንት ነው።(ዮሐ 5፣1)

በኢየሩሳሌም በእብራይስጥ ትርጓሜዋ የምህረት ቤት የሆነ ቤተ ሳይዳ የምትባል መጠመቂያ ነበረች። ይህችም መጠመቂያ አምስት መመላለሻ ነበረባት። በዚህች መጠመቂያ የጌታ መልአክ ይወርድና ውሃውን ያናውጣል። በተናወጠ ጊዜ ቀድሞ የገባ በሽተኛ ከማንኛውም ደዌ ይፈወሳል።

አምስቱ መመላለሻ የአምስቱ አዕማደ ምስጢር ምሳሌዎች ናቸው። መልአኩ የሚወርደው ለቀድሶ ማያትና(ውሃውን ለመባረክ) ለአዕርጎ ጸሎት(ጸሎት ለማሳረግ) ነው። መልአኩ ሲወርድ ውሃው መናወጡ መልአኩ እንደወረደ ለማጠየቅ ነው።
ለምን ቀድሞ የገባ ይድናል ቢሉ በኦሪት ፍፁም ድኅነት አልነበረምንና ነው እንዲሁም በቀን አንድ አንድ መፈወሱ የእግዚአብሔር ምሕረት ፍፁም አለመራቁን የሚያሳይ ነው።

በዚህች ቦታ ነበር መፃጉዕ ለ 38 ዓመት በህመም እየተሰቃየ ውሃው በተናወጠ ጊዜ ወደ ውሃው የሚያስገባው ሳይኖር አንድ ቀን እድናለሁ በሚል ተስፋ ሲጠባበቅ የኖረው። የሚገርመው ይህ ሰው ጌታችን ሳይወለድ በፊት በዚህ ቦታ ነበር። ሁሉን በጊዜው ውብ አድርጎ የሚሰራው አምላካችን የመፃጉ የመዳን ቀን ደረሰና ሊያድነው ወደርሱ መጣ።

ኢየሱስም ይህን ሰው ተኝቶ ባየ ጊዜ እስካሁን ብዙ ዘመን እንዲሁ እንደነበር አውቆ “ልትድን ትወዳለህን ?” አለው።
ምንም ነገር ከእርሱ የማይወጣው አምላካችን እንዲህ ብሎ መጠየቁ “ምን ጥያቄ ያስፈልገዋል” ሊያስብል ይችላል። ነገር ግን ለእርሱ ብቻ ሳይሆን ጌታችን ይህን ጥያቄ በሌላ ቦታ ሲጠይቅ እናያለን።(ማቴ 22፤32 ሉቃ 18፤41) ታድያ ምን እንደምንፈልግና እንደሚያስፈልገን እያወቀ መጠየቁ ለምንድር ነው? ቢሉ አንድም የሰው ሥጋ መልበሱን ለማጠየቅ (አላዋቂ የሆነን ስጋ መልበሱን) ፤ አንድም ነፃ ፈቃድ ያለን ሆነን ተፈጥረናልና ለማዳንም ቢሆን ፈቃዳችን ላለመንፈግ ፤አንድም በዕለተ ዓርብ በጥፊ የሚመታው ነውና “ያዳነህን ?” ባሉት ጊዜ “አድነኝ ብዬዋለሁ ?” እንዳይል ፤ አንድም ደግሞ ለድኅነታችንም ለኃጢአታችንም ኃላፊነት መውሰድ እንዳለብን ሲያስረዳ ነው።(ዘፍ 3፣9/ 4፤9)

መፃጉም መልሶ ይረዳኛል ወይም አንዱን ያዝልኛል ብሎ በማሰብ “ወደመጠመቂያው የሚወስደኝ የለም እኔ በደረስኩ ጊዜ ሌላው ይቀድመኛል” ብሎ መለሰለት ማን እንደሆነ አላወቀምና። ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው “ተነሳና አልጋህን ተሽክመህ ሂድ” ወዲያውም ሰውየው ዳነ አልጋውንም ተሸክሞ ሄደ።

ጌታችን ያዳነበት መንገድ እጅግ የሚደንቅ ነበር። ምክንያቱም ለ 38 ዓመት እድናለሁ ብሎ ይጠብቀው በነበረው ጠበል ሳይሆን በቃሉ ብቻ “ተነስ” በማለት ነበር። ይህንንም ይደረገው አንድም ቅድም ሥጋን መልበሱ ለማጠየቅ ልትድን ትወዳለህ እንዳለው እንዲሁም መለኮት ደግሞ ሥጋን እንደተዋሃደ ለማጠየቅ በቃሉ ብቻ “ተነስ” ብሎ 38 ዓመት የተኛበትን አልጋ እንዲሸከም ጭምር አዝዞት ድንቅ ተአምር አድርጓል። አንድም ደግሞ በጠበሉ ቢያድነው ከእግዚአብሔ አዳኝነት ይልቅ የእርሱ ይህን ሁሉ ዓመት መጠበቁ ይህን ድሕነት እንዳስግኘለት በማሰብ እንዳይመጻደቅ የሰው ድርሻ ፈቃድ ማዳን ደግሞ የእግዚአብሒር መሆኑን ለማስረዳት ነው።

ዛሬም እንደ መፃጉዕ ሰው አጥተው በየሆስፒታሉ ፣ በየፀበሉ ፣ በየቤታቸው የሚሰቃዩ ብዙዎች ናቸው። የመፃጐዕም ሰው ማጣትም 38 ዓመት አስጠብቆታል እናም ቅድስት ቤተክርስቲያናችን እኒህን ችግረኞች ማሰብና መርዳት እንዳለብን እንደ ሁል ጊዜው በተለይ በዚህ ሳምንት አምልታና አስፍታ የዳዊትም መዝሙር እንዲህ እያለች እየዘመረች ትሰብካለች። “ለችገረኛና ለምስኪን የሚያስብ ምስጉን ነው እግዚአብሔር ከክፉ ቀን ያድነዋልና” (መዝ 40፤1)

ብዙዎቻችን ደግሞ በደዌ ነፍስ እየተሰቃየን ነው። የነፍስ በሽታዋ ደግሞ እግዚአብሔርን ማጣቷ ነው። እርሱ የሚጠይቀን ፈቃዳችንን ብቻ ነው።(1ጢሞ 2፤3) በንስሐ በመታጠብ ልጅነታችንን እንድንጠብቅ አምላከ ቅዱሳን ይርዳን።

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር።
ዲ/ን ናትናኤል
መጋቢት 3/2015 አዲስ አበባ/ኢትዮጵያ

 #ምኩራብ“የቤትህ ቅናት በልታኛለችና የሚሰድቡህም ስድብ በላዬ ወድቋልና ነፍሴን በጾም አስመረርኋት” መዝ ፷፰-፱ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ የዐቢይ ጾም ሳምንታትን እንደሰየመው ሦስተኛው ሳ...
05/03/2023

#ምኩራብ
“የቤትህ ቅናት በልታኛለችና የሚሰድቡህም ስድብ በላዬ ወድቋልና ነፍሴን በጾም አስመረርኋት” መዝ ፷፰-፱

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ የዐቢይ ጾም ሳምንታትን እንደሰየመው ሦስተኛው ሳምንት በርእሱ እንደተገለጸው ምኩራብ በመባል ይታወቃል።

ምኩራብ (synagogue)አይሁዶች አምልኮ ለፈጣሪ የሚያቀርቡበት (የጸሎት) ስፍራ ነው። አይሁዶች አምልኮዋቸውን ይፈጽሙ የነበረው ኢየሩሳሌም በሚገኘው ቤተ መቅደስ ነበር። ንጉስ ናቡከደነፆር በጦርነት ቤተ መቅደሳቸውን አፍርሶ ሕዝባቸውንም ማርኮ ወደ ባቢሎን ከወሰደ ጊዜ ጀምሮ አይሁድ በሚኖሩባቸው ስፍራዎች ሁሉ ለጸሎትና ለአምልኮ ልዩ ቤት መሥራት እንደጀመሩና ስሙንም ምኩራብ እንዳሉት ይነገራል። (ሕዝ 11፤16) በዚህም ቦታ አይሁዶች ይጸልያሉ ፣ ይማራሉ ፣ ያስተምራሉ ከመስዋዕተ ኦሪት በቀር የቀረውን ሥርዓተ አምልኮ ይፈጽሙ ነበር። ነገር ግን መስዋዕት ለማቅረብ የግድ ወደ ኢየሩሳሌም መሄድ ይጠበቅባቸው ነበር።

አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በመዋዕለ ሥጋዌው በዚህ ምኩራብ እየሄደ ያስተምር ነበር። (ሉቃ 4፤16 ማር 6፤1)

ቅዱስ ያሬድም ስለዚህ ሳምንት በጾመ ድጓው ድርሰቱ ላይ እንዲህ ሲል ዘምሯል፦ “ቦአ ኢየሱስ ምኩራቦሙ ለአይሁድ ወመሐረ ቃለ ሃይማኖት ወይቤሎሙ ምጽዋተ አበድር እመሥዋዕት አነ ውእቱ እግዚኣ ለሰንበት ወአቡሃ ለምሕረት እግዚኣ ውእቱ ለሰንበት ወልደ እጓለ እመሕያው ኢትግበሩ ቤተ አቡየ ቤተ ምስያጥ ቤትየሰ ቤተ ጸሎት ይሰመይ ቦአ ምኩራቦሙ ወገሠፆሙ ያርምሙ አንከሩ ምህሮቶ ሞገስ ቃሉ ወጣዕመ ነገሩ ወሣዕሣዓ አፉሁ፡፡
ትርጉም:- ጌታችን ኢየሱስ ወደ አይሁድ ምኩራብ ገባ፤ የሃይማኖት ቃልን አስተማረ፤ ከመሥዋዕት ይልቅ ምሕረትን እወዳለሁ፤የሰንበት ጌታዋ የምሕረት አባቷም እኔ ነኝ፤ የሰው ልጅም የሰንበት ጌታዋ ነው ፡፡ያባቴን ቤት የንግድ ቦታ አታድርጉት፤ቤቴስ የጸሎት ቤት ይባላል (እያለ የሃይማኖትን ቃል አስተማራቸው፡)፡ ወደ ምኩራባቸውም ገብቶ ዝም ይሉ ዘንድ ገሠፃቸው፤ እነርሱም ትምህርቱን፣ የቃሉን ግርማ፣ የአነጋገሩን ጣዕምና፣ የአንደበቱን ቅልጥፍና አደነቁ”

ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት “የቤትህ ቅናት በልታኛለችና የሚሰድቡህም ስድብ በላዬ ወድቋልና ነፍሴን በጾም አስመረርኋት” (መዝ ፷፰-፱) ያለው ትንቢት በዚህች ቀን ይሰበካል።

ከወንጌል ክፍልም የሚነበበው ስለ ቀኑ የሚናገረውን ጌታችን ምኩራብ በተባለች ቤተመቅደስ ይሸጡና ይለውጡ የነበሩትን በጅራፍ እየገረፈ “ቤቴ የጸሎት ቤት ይባላል እናንተ የወንበዴውች ዋሻ አደረጋቹት” ብሎ እንደገሰጻቸው ደቀመዛሙርቱም “የቤትህ ቅናት በላኝ” ብሎ ዳዊት የተናገረው ትንቢት መፈፀሙን ማስታወሳቸውን የሚናገረው የወንጌል ክፍል ነው። (ዮሐ 2፤12-25 )

በወንጌሉ ላይ የተገለጸችው ምኩራብ የዛሬይቷ ቤተ መቅደስ ምሳሌ ነች። አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደቤተመቅስ ገብቶ ይህን ያደረገው በተራራው ስብከቱ “እኔ ሕግንና ነቢያትን ለመሻር የመጣሁ አይምሰላችሁ ፤ ልፈጽም እንጂ” (ማቴ 5፤17) ብሎ እንደተናገረው አይሁዶች እንደሚሉት ቤተ መቅደሱን ለማፍረስ ሳይሆን መሥዋዕተ ኦሪትን አስወግዶ የመቅደሱን ሥርዓትና አገልግሎት ፍጹም ለማድረግ እንዲሁም በሬ ፤ በግ ፤ ርግብ ይሸጡ የነበሩትን በማስወጣት በእነዚህም ይፈጸም የነበረው መሥዋዕተ ኦሪት ማለፉን እናም በእርሱ ሥጋና ደም መለወጡን እንዲሁም የሚሠዋበት ጊዜ መድረሱን ለመንገርም ጭምር ነው።

አንድም መቅደስ (ምኩራብ) የተባለው የእግዚአብሔር መንፈስቅዱስ ማደርያ የሆነው የእኛን ሰውነት ይመለከታል። (1ኛ ቆሮ 3፤17 ፤ 1ኛ ቆሮ 6፤19 ፤ 2ኛ ቆሮ 6፤16)

ቤተክርስቲያናችንም በዚህ ሳምንት እኛ ክርስቲያኖች ለእርሱ ማደርያነት እንመች ዘንድ ሸቀጥ የተባለውን ኃጢያታችንን አስወግደን በንስሐ ታጥበን ንጹህ እንድንሆን ትሰብካለች። እንዲሁም ለመቅደሱ ሥርዓት መገዛት ሲያቅተን ሥርዓቱን ለራሳችን አኗኗር እንዲመች አድርገን ሥርዓቱን ማበላሸት ሳይሆን ቅዱስ ጳውሎስ እንዳለው “የእግዚአብሔር ፈቃድ እርሱም በጎና ደስ የሚያሰኝ...” ነውና “ፍጹምም የሆነው ነገር ምን እንደሆነ ፈትናችሁ ታውቁ ዘንድ በልባችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህን ዓልም አትምሰሉ” እንዳለው ይህን ዓልም መምሰል እንደሌለብን ቅድስት ቤተክርስቲያናችን ታስተምራለች።(ሮሜ 12፤2)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር።
ንዋየ ወርቅ-Newaye werqe
የካቲት 26/2015

26/02/2023

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ ። አምላክ አሜን !
እንኳን ለዐቢይ ጾም ሁለተኛ ሳምንት በሰላም አደረሳችሁ!

ቅድስት
እንደ እግዚአሔር ፈቃድ “ዘወረደ” ተብሎ የተሰየመውን የዐቢይ ጾም የመጀመሪያውን ሳምንት ጨርሰን ወደ ሁለተኛው ተሸጋግረናል። ሁለተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት በርእሱ እንደተገለጸው ቅድስት በመባል ይታወቃል። እኚህን የጾሙን ሳምንታት የሰየመው ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ነው።

ቅድስት የሚለው ቃል ሲፈታ ልዩ ፤ ጽሩይ ፤ ክቡር የሚለውን ትርጉም ይሰጣል። ይህ የዐቢይ ጾም ሁለተኛ ሳምንት ጌታ ጾም የጀመረበት የመጀመሪያ ሳምንት ነው። (ዘወረደ ተብሎ የሚጠራው የመጀመሪያ ሳምንት አምላካችን ከሰማያት መውረዱን የሰውን ሥጋ መልበሱን ፤ መወለዱን እያሰብን የምንጾመው ነው።)

ቅድስና የባሕርይ ገንዘቡ የሆነ አምላካችን ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አዳምና ሔዋን ዕፀ በለስ በመብላታቸው በሰው ዘር የመጣውን ዕዳና በደል ደምሰስ እንዲሁም ለአዲስ ኪዳን ትውልድም ሥርዐተ ጾምን ለማስተማር መጾም የጀመረበት የመጀመሪያ ሳምንት ስለሆነ ቅድስት ተብሏል።

እከብር አይል ክቡር ፤ እቀደስ አይል ቅዱስ ፤ እነግስ አይል ንግሥና የባሕርዩ የሆነ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በልዩ አመጣጡ ሥጋችንን ተዋህዶ ከርኩስነት ሊያነጻን ፤ አንድም አዳም በምግብ ምክንያት ከክብሩ ተዋርዶ ነበርና በአዳም ቦታ ገብቶ ካሳ ሊከፍል ፤ አንድም ለኛ ምሳሌና አርአያ ለመሆን ጾሞልናል። እርሱ ቅዱስ እንደሆነ ሁሉ የቅድስናን ሕይወት በተግባር ሊያሳየን እንዲሁም የቅድስናን መንገድ የሚቃወመው ዲያቢሎስን እንዴት ድል ማድረግ እንደምንችል እና እንዲሁም ድል ሊነሳልን ጾሞልናል።(1ኛ ጴጥ 1፤15)(ማቴ 4፤1-14 ፤ማር 1፤14-15 ሉቃ 4፤14-15)

በዚህችም ሰንበት የሚሰበከው ምስባክ ነብየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት እግዚአብሔር ቅድስና የባሕርይ መሆኑን ሲናገር “እግዚአብሔርሰ ሰማያተ ገብረ አሚን ወሰናይት ቅድሜሁ ቅድሳት ወዕበየ ስብሐት ውስተ መቅደሱ -የአሕዛብ አማልክት ሁሉ አጋንንት ናቸው እግዚአብሔር ግን ሰማያትን ሰራ ምስጋናና ውበቱ በፊቱ ቅድስናና ግርማ በመቅደስ ውስጥ ናቸው።” የሚለው ነው። (መዝ 95፤5)

እንዲሁም ከወንጌል ክፍል አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተራራው ስብከቱ ላይ ስላ አንቀጸ ጾም ካስተማረው “ስትጦሙ እንደግብዞች አትጠውልጉ ሰዎች እንደጦመኛ ሊታዩ ፊታቸውን ያጠፋሉና እውነት እላችኃለሁ ዋጋቸውን ተቀብለዋል። አንተ ግን ስትጾም በስውር ላለው አባትህ እንጂ እንደጦመኛ ለሰዎች እንዳትታይ ራስህን ተቀባ ፊትህንም ታጠብ በስውር የሚያይህ አባትህ በግልጥ ይከፍልኃል። ” (ማቴ 6፤16-19) የሚለው ነው።

በዚህ የወንጌል ክፍል ውስጥ ቤተክርስቲያን የምታስተላልፈው መልዕክት ምንም እንኳን ጾሙ የአዋጅ ጾም ቢሆንም ስንጾም ሰው እንዲያውቅልንና ዋጋቸውን ቀብለዋል እንደተባሉት ግብዞቹ ወዳሴ ከንቱ ሽተን ሳይሆን ሰማያዊውን ዋጋ ለማግኘት ስንል መሆን አለበት።

#ራሳችሁን ተቀቡ ሲል አንድም ፍቅርን ያዙ ሲል ነው ቅዱስ ጳውሎስ ወደ ቆሮንቶስ በላከው መልዕክቱ ላይ “በሰዎችና በመላዕክት ልሳን ብናገር ፍቅር ግን ከሌለኝ እንደሚጮህ ናስ ወይም እንደሚንሿሿ ጸናጽል ነኝ ...ተራራዎችን እስካፈልስ ድረስ እምነት ቢኖረኝ ፍቅር ከሌለኝ ከንቱ ነኝ..”(1ኛ ቆሮ 13፤ 1-2)
በማለት ፍቅር የሌለብት ነገር ሁሉ ከንቱ እንደሆነ ገልጾልናል። አንድም ደግሞ ንጽህናን ገንዘብ አድርጉ ትህትናን ያዙ ማለቱ ነው።

#ፊትህን ታጠብ ማለቱ ደግሞ በአንብአ ንስሐ ታጠቡ ማለቱ ነው። በንጽህና ሆንችሁ ጹሙ ሲል ነው። በፍቅር ፤ በንጽህና በትህትና ያልታጀበ ጾም ከንቱ ነውና ። ስለዚህ በእግዚአብሔር የተወደደ ጾም እንዲሆን በትንቢተ ኢሳይያስ እንደተገለጸው መሆን አለበት። “..እኔስ የመረጥኩት ጾም ይህ አይደለምን? የበደልን እስራት ትፈቱ ዘንድ ፤ .የተገፉትን ሐራነት ትሰዱ ዘንድ ቀንበሩን ሁሉ ትሰብሩ ዘንድ አይደለምን ..እንጀራህን ለተራበ ትቆርስ ዘንድ ስደተኞችን ደሃዎችን ወደ ቤትህ ታገባ ዘንድ ... የዚያን ጊዜ ብርሃንህ እንደ ንጋት ይበራል፤ ፈውስም ፈጥኖ ይበቅላል ጽድቅም
በፊትህ ይሄዳል የእግዚአብሔር ክብር ከኋላህ ሆኖ ይጠብቅሃል ”
(ኢሳ 58፤3 ዘካ 7፤5)

ዲ/ን ናትናኤል
አዲስ አበባ ፤ ኢትዮጵያ
የካቲት /19/2015
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር

እንኳን ከዘመነ ማርቆስ ወደ ዘመነ ሉቃስ በሰላም አሽጋግራችሁ!ሃይማኖታችን እንደሚያስተምረን ዘመን መጀመሪያ መጨረሻም የለውም። “የባህር አሸዋን የዝናም ጠብታን የዘመንን ቁጥር ማን ቆጠረ።”(...
11/09/2022

እንኳን ከዘመነ ማርቆስ ወደ ዘመነ ሉቃስ በሰላም አሽጋግራችሁ!

ሃይማኖታችን እንደሚያስተምረን ዘመን መጀመሪያ መጨረሻም የለውም። “የባህር አሸዋን የዝናም ጠብታን የዘመንን ቁጥር ማን ቆጠረ።”(ሲራ 1፤2)መጨረሻ የሌለው ነገር ታድያ እንዴት ይቆጠራል ብንል መቁጠር የተጀመረው ከአዳም መፈጠር በኋላ መሆኑን ሊቃውንተ ቤ/ን ያስተምራሉ። አበው የሚያስተምሩት “ዓለም ታልፋለች” እያሉ እንጂ ዘመን ያልፋል አይሉም። ዘመን ዓለም ከመፈጠሩ በፊት ነበር ፤ ዓለም ካለፈም በኋላም ይኖራል። በዚህ መሠረትም “እግዚአብሔር ዘመንን በአምሳሉ ፈጠረው” ብንል ለመረዳት ይቀላል።

እግዚአብሔር አምላካችን ረቡዕ በፈጠራቸው ፍጥረታት ፀሀይ ፤ ጨረቃና ከዋክብት መዓልቱን ከሌሊት ፣ ዓመቱን ከዘመን ይለዩ ዘንድ ሹሟቸዋል።(ኩፋ 2፤13) የፀሀይ ብርሃን የሚታይበት እና የማይታይበት ዘመን ተደምሮ አንድ ዕለት እንላለን። የፀሀይ ብርሃን የሚታይበት በግዕዝ መዓልት በአማርኛ ቀን ይባላል። የፀህይ ብርሃን የማይታይበት (ጨለማው)በግዕዝም በአማርኛም ሌሊት ይባላል።

#አዕዋዳት

ዓለም ከተፈጠረ አንስቶ እስከ ልደተ ክርስቶስ ያለው ዘመን ዘመነ ብሉይ ፣ ዓመተ ፍዳ ፣ ዓመተ ኩነኔ ይባላል። ከልደተ ክርስቶስ ወዲህ ያለው ዘመን ዓመተ ምህረት ፣ ዓመተ ሥጋዌ ፣ ዘመነ ሐዲስ ይባላል። መላው ዓመተ ዓለም ይባላል። ብዙ ጊዜ አውድ ሲባል በአእምሮአችን የሚመጣው አውደ ዓመት ነው። ነገር ግን አዕዋዳት ብዙ ብዙ ናቸው። አውድ ማለት እንደ ቀለበት ያለ ክብ ዙሪያ ገጠም ወይም ዙሮ መምጣት የሚችል ፤ ምልሰት ማለት ነው። በሌላም አነጋገር አውድ መካተቻ መሰብሰቢያ ፤ መቆሚያ ትብሎ ይተረጎማል። እነዚህም መቁጠሪያዎች (መለኪያዎች) ምልሰት (recycle) ስለሚያደርጉ ዓውድ ተብለዋል። ዓውድ በብዙ ሲሆን ደግመ አዕዋድ ይሆናል። እነዚህ አዕዋዳትም በ7 ዓበይት ክፍሎች ተከፍለው ለዘመንአቆጣጠር ስልት እንደ መሠረትነት ያገለግላሉ። እነርሱም፦

(24 ሰዓት)፡ ከእሁድ እስከ ቅዳሜ ያሉት ዕለታት ምልልስ ነው።

(ወር)(28/29 ቀን)፡ ወርኅ የግዕዝ ቃል ሲሆን ትርጉሙ ጨረቃ ማለት ነው። የወር አቆጣጠር አንድ ጊዜ 29 አንድ ጊዜ 30 ሲሆን በፀሐይ አቆጣጠር ግን ሁል ጊዜ 30 ነው።
ዓውደ ዓመት፡ በፀሐይ አቆጣጠር 365 ቀን ከ5 ሰዓት ከ48 ደቂቃ ከ46 ዳግሚት(second)ነው። በጨረቃ አቆጣጠር ደግሞ 354 ዕለታት ናቸው። የጨረቃ ዓውደ ዓመት ከፀሐይ በ11 ያነስችው የማትታይበት ጊዜ ሰላለ ነው።

(በየ 19 ዓመት የሚመላለስ መስፈርያ ነው።)፡ አበቅቴ ማለት ተረፈ ዓመት ማለት ነው። ይህም በአንድ ዕለት ውስጥ ያሉትን የሌሊቱንና የጨረቃውን ኅድረት (ቆይታ) ከመዓልቱ (ከቀኑ) ለይቶ ለማወቅ ያስችላል።

(በየ 76 ዓመት የሚመላለስ መስፈርያ ነው።)፡ ይህም ወንጌላውያንንና አበቅቴን ለማግኘት የሚረዳ ነው።

(በየ 532 ዓመት የሚመላለስ መስፈርያ ነው ወንጌላዊ ዕለትና አበቅቴን ይገኝበታል።

(28 ዓመት ነው)
የዘመን አቆጣጠር በኢትዮጵያውያን አሰያየም ባሕረ ሀሳብ ይባላል።

?
ባሕረ ሓሳብ የግእዝ ቃል ሲሆን በዐረብኛ አቡሻህር በአማርኛ የዘመን አቆጣጠር ይባላል። ስለ ምን ዘመንን ባሕር አለው ? ቢሉ ባሕር ከምንጩ ወጥቶ ቢፈስ አያልቅም ዘመንም ምጽአተ ክርስቶስ እስኪያግደው ድረስ ሰውን እያሳለፈ ሲመላለስ ይኖራል። አንድም ከባሕር ሁከት እንዳይታጣ ፣ ከዘመንም ሁከተ ሥጋ ሁከተ ነፍስ አይታጣምና። አንድም ከባሕር ማዕበል፣ ሞገድ እንዲነሳሳ ከዘመንም ማዕበለ ኃጢአትና ማዕበለ ክህደት ይነሳልና። መልሕቅ ጥለው ከባሕር ማዕበል ፀጥ እንዲያደርጉ ፤ ክህደትንም ጹመው ጸልየው ምህላ ይዘው ፀጥ ያደርጉታልና። አቆጣጠሩ ባሕረ ሓሳብ ተብሏል።

እንደ ቤተክርስቲያናችን አተምህሮና መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚለን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሰው ልጆች ቤዛ ሆኖ በመለዕልተ መስቀል የተሰቀለው በዕለተ ዓርብ ነው። በሦስተኛውም ቀን በዕለተ እሁድ ከሙታን ተለይቶ ተነስቷል። የክርስቶስን ትንሳኤ ፋሲካ የምንለው ለክርስቶስን ሕማምና ትንሳኤ ትንቢት ስለነበረው ነው። 318ቱ ቅዱሳን ጳጳሳት በኒቂያ ጉባኤ ካስተላለፉት ውሳኔዎች መካከል የትንሳኤ በዓል ሁል ጊዜ እሁድ እንዲውል ነበር። ምክንያታቸውም ክርስቶስ የተሰቀለው የአይሁድ ፋሲካ(ከግብፅ ባርነት የወጡበትን የሚያከብሩት በዓል) እንደተበላ ነው። ይህ ማለት ክርስቶስ የተሰዋበትንና ከሙታን ተለይቶ የተነሳበትን ለማስታወስ ሁል ጊዜ የአይሁድ ፋሲካ የሚውልበት ማወቅ ያስፈልጋል። በዚህም ምክንያት የአይሁድ ፋሲካ ከዋለበት ቀን በኋላ የሚመጣውን እሁድ የትንሳኤ እሁድ እንዲሆን ወሰኑ። ነገር ግን ይህን ውሳኔ ለመጠበቅ ክርስቲያኖች ላይ ችግር ፈጥሮባቸው ነበር። ችግሮቹም፦

#1️_የዘመን_አቆጣጠር_ልዩነት ነው።
ክርስቲያኖች የሚቆጥሩት በፀሐይ አቆጣጠር ሲሆን አይሁዶች ግን የሚቆጥሩት በጨረቃ(በወርኅ) ነው። ይህ ደግሞ ልዩነት ፈጥሯል።

ክርስቲያኖች ጠብ ነው።
ክርስቲያኖች ከአይሁድ ሃይማኖት የክርስቶስን መምጣትና የድኅነት ሥራ መፈጸሙን አምነው ከአይሁዶች ስለተለዩ በመካከል ጠብ ተፈጥሮ ነበር። የክብርን ጌታ ስለሰቀሉና በእነርሱም ስደትና ጭቆና አብዝተውባቸው ስለነብር የፋሲካ በዓላቸውን ከነርሱ ጋር ላለማክበር ወሰኑ።

ስለዚህም ምክንያት ከፀሐይ አቆጣጠር ጋር የሚስማማና የጌታችንንም ትንሳኤው ወቅቱን እንዲጠብቅ የሚያደርግ የዘመን አቆጣጠር ያስፈልግ ነበር። ይህንንም መልስ የመለሰው ባሕረ ሓሳብ ነው።
ይህን የዘመን ቀመር የቀመረው 12ኛው የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ዲሜጥሮስ ነው። ቅዱስ ዲሜጥሮስ፦
-ነነዌ እና ጾመ ሐዋርያት ፦ ከሰኞ
-ደብረ ዘይት ፣ ሆሳዕና ፣ ትንሳኤ፤ ጰራቅሊጦስ ፦ ከእሁድ
-ጾመ ድኅነት ፦ ከረቡዕ
-ዕርገት፦ ከሐሙስ
-ስቅለት፦ ከዓርብ
ባይወጡ እያለ ይመኝ ነበር። ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ መጥቶ ሱባኤ እንዲገባ ያዘዋል። ቅዱስ ዲሜጥሮስም በሱባኤ እግዚአብሔርን ጠይቆታል። በዚህ ሲመኝ የነበረው ተገልጾለት ከላይ ባየናቸው በተዘረዘሩት ሰባት አዕዋዳት አውዶ በሶርያ ፤ በአንጾክያ ፤ በሮምና በኢየሩሳሌም ላሉት ሊቃነ ጳጳሳት ጽፎ ላከላቸው። እነርሱም ተቀብለው አስተምረውታል።

ወደ አገራችን የዘመን አቆጣጠር ስንመጣ የኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር ኦሪታዊያን የሙሴ ሕግ የተከተለና የሊቀ ጳጳስ ዲሜጥሮስ ቀመር የተላበሰ ቢሆንም ራሱን የቻለ የቀደመ ሂደት ያለውና ከጥንት እየተሰራበት የመጣ በመሆኑ ከምዕራባውያን የዘመን አቆጣጠር ተለይቷል።

የኢትዮጵያ የዘመን መለወጫ /ርዕሰ ዓውደ ዓመት/ በየዓመቱ መስከረም አንድ ቀን ነው። ከልደተ ክርስቶስ በኋላ ዓውደ ዓመቱ የሚውልበት ዕለት ዮሐንስ የሚል ስያሜ ተሰጥቶታል። ይህም ብሂል በዘመነ ሐዲስ ለዮሐንስ መጥምቀ መለኮት የተሰጠው ለወንጌል ትምህርት የመጀመርያው መንገድ ጠሬጊ /ማር 1 ፤40፤ ኢሳ 40 ፤ 3- 4/በመሆኑና አዲስ የህይወት መንገድን ብሥራት በማብሠሩ ከአዲሱ ዓመት ጋር በየዓመቱ እንዲታሰብ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት ሊቃውንት ታምኖበት ተሰጥቶታል፡፡

የአገራችን ታላቁ የዜማ ደራሲ ቅዱስ ያሬድም የዮሐንስን ተልዕኮ በተመለከተ ከመስከረም 1 ቀን ከዋዜማው ላይ "ብፁዕ አንተ ዮሐንስ ዘሀለወከ ታእምር” ትርጉም ማወቅ እና ማሳወቅ የተሰጠህ ዮሐንስ አንተ ክቡር ነህ" ብሎ ገልጾታል፡፡ የመስከረም ወር በኢትዮጵያውያን ዘንድ አዲስ ዘመን የሚቆጠርበት ለአዲስ ሕይወት ምዕራፍ ጽንሰ ኃሳብ የሚነደፍበትና ዕድሜ የሚቆጠርበት ነው። ዓውደ ዓመቱ በክረምቱ ክፍለ ጊዜ ቢሆን ዓመቱ በአራት ተመድቧል፡፡ ማለትም

#ከመስከረም 26 ዕለት እስከ ታኅሣሥ 25 ያለው ዕለት መፀው (የመኸር ወራት )

#ከታኅሣሥ 26 ዕለት እስከ መጋቢት 25 ያለው ዕለት ሐጋይ(የበጋ ወራት)

#ከመጋቢት 26 ዕለት እስከ ሰኔ 25 ዕለት ጸደይ (የበልግ ወራት )

#ከሰኔ 26 ዕለት እስከ መስከረም 25 ዕለት ክረምት (የዝናም ወራት) እየተባለ ይጠራል፡፡

ይህም አከፋፈል የኢትዮጵያን የሀገሪቱን ወቅታዊ የአየር ጠባይ እና የተፈጥሮን ሕግጋት የተከተለ ብቸኛ ሕግ ሲሆን ከጥንት ዓመተ ዓለም ጀምሮ በይዞታዋ ጠብቃ ያቆየችው የግሏ የታሪክ ቅርሷ ነው፡፡

#የ"ዕንቁጣጣሽ" አመጣጥ
ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን እንደሚያስረዱት ዕንቁጣጣሽ የሚለው ስያሜው አመጣጥ ወይም ጥንተ ታሪክ በመጀመሪያ ኖኅ ለሦስቱ ልጆቹ አህጉራትን በዕጣ ሲያካፍላቸው አፍሪቃ ለካም ደረሰችው፡፡ በአፍሪቃ ምድርም ሲገባ በመጀመሪያ ያረፈው በኢትዮጵያ ነበር፡፡ ሀገሪቱም በአደይ አበባ አሸብርቃ ነበር፡፡ ወሩ ወርኃ መስከረም በመሆኑ ደስ ብሎት «ዕንቁ ዕጣ ወጣሽልኝ» ይህችን ወቅት እንቁጣጣሽ ብሏታል፡፡

ሁለተኛው የሀገራችን ንግሥት ንግሥተ ሳባ የንጉሥ ሰሎሞንን ዜና ጥበብ እየሰማች ስታደንቅ ትኖር ነበር፡፡ በጆሮዋ የሰማችውን በዓይኗ ዓይታ ለመረዳት ስለፈለገች ከብዙ ስጦታዎች ጋር ወደ ኢየሩሳሌም ገባች፡፡ ከንጉሡ ሰሎሞንም ጋር ተገናኝታ የያዘችውን ገጸ በረከት ከሰጠችው በኋላ ብዙ ነገሮችን ጠየቀችው፡፡ ቤተ መንግሥቱንም፣ በቤተ መንግሥቱ የሚገኙ እጅግ በጣም የከበሩ ዕቃዎችን ሁሉ አስጎበኛት፡፡ ሲያበቃ «ዕንቁ ለጣትሽ ጌጥ ይሁንልሽ» ሲል እጅግ በጣም የከበረ ዕንቁ አበረከተላት/ሰጣት/፡፡ ወሩም ወረኃ መስከረም ነበር፡፡ ከዚህ በመነሣት እንቁጣጣሽ የሚለው መጥቷል፡፡ አንድም «ዕንቁ ዕፅ አወጣሸ» ብሎ የአበባውን መፈንዳትን ያስረዳናል፡፡

#በአዲሱ ዓመት ምን አስብህ/ሽ?

ለሁላችንም እኩል የተሰጠና አድልኦ አለበት ብለን ልንከራከር የማንችለው ነገር ቢኖር ውዱ ጊዜያችን ነው። አምላካችን እግዚአብሔርም እንደ ቸርነቱ ብዛት የምህረት ዓመትን ያቀዳጀናል። መዝ 64/65፤11 ተረታችን እንደሚለው ሰው ሆኖ ከኃጢአት ብረት ሆኖ ከዝገት የሚያመልጥ የለምና ሰውነታችንን ሁል ጊዜ በሳሙና እንደምንታጠብ ሳሙና በተባለው ንስሐ ልንታጠብ ያስፈልገናል። ወዳጄ በአዲሱ ዓመት ምን አስበሃል ? ቤት መስራት ፣ መኪና መግዛት ፣ ትዳር መያዝ ፣ ማትረፍ ፣ መነግድ ? ግን ወዳጄ አስቀድመህ የእግዚአብሔርን መንግስትና ጽድቅ ፈልግ ይህ ሁሉ ይጨመርልሃል። ማቴ 6፤33 ወደ ጽድቅ መንገድ የምትመራው የመጀመሪያ በር ደግሞ ንስሐ ናት። አስብ ህይወታችን ጥቂት ጊዜ ታይቶ እንደሚጠፋ እንፋሎት ነው። በዚህ ፈንታ ጌታ ቢፈቅድ ይህን አደርጋልሁ በል። ንስሐ እገባለሁ ፣ ስጋና ደሙን እቀበላለሁ ፣ ቃሉን እማራልሁ ፣ በጸሎቴ እበረታለሁ፣ ከአልባሌ ቦታ እርቃልሁ በል (ያዕ 4፤13፦15)፤ ምክንያቱም የጌታ ፈቃድ መልካምና ደስ የሚያሰኘው ከኃጢአት ተለይተህ ንስሐ ገብተህ ትድን ዘንድ ነውና። 1ኛጢሞ 2፡3፦4 ልብስህ ሲቆሽሽ መልስህ እንደምታጥብ መልስህ ብትበድልም መልሰህ ነስሐ ግባ! ቤተ/ን ሂደህ አትውቅም ? መመለሻው ጠፋህ? አይዞህ ከ አባት በላይ የሆነ አባት አለህ ገና ከሩቅ ሲያይህ ደስ ብሎት ሊቀበልህ የሚወጣ አባት አለህ። ወዳጄ አባትህ እጀጉን ናፍቆሃል። የጠፋው ልጄ ምን ሆኖ ይሁን እያለ ነው። አባክህ ናለት አባቴ ይቅር በለኝ በድያልሁ፤ ልጅህ ልባል አይገባም በለው ወድቀህ እግዱ ስር ለምነው። አይጨክንብህም ይቅር ይልሃል። ቅረብ ያበራልሃል። ያዕ 4፡8 መዝ 34/35፡5 አዲሱ ዓመት የሰላም ፣ የጤና ፣ የፍቅር ፣የንስሐ ፣ የጸሎት ፣ የምስጋና እንዲሆን የአምላክችን ቅዱስ ፈቃድ ይሁንልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር።

ለሁሉ ይዳረስ ዘንድ ያጋሩ ፡፡

13/08/2022

[ነሐሴ 7 ፅንሰታ ለማርያም (የአምላክ እናት የተፀነሰችበት)]
✍ በመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ
❖ ነሐሴ 7 የአምላክ እናት የፅንሰቷ በዓል በቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ይከበራል። በነገረ ማርያም ላይ እንደተጻፈ በእናቷ በሐና በኩል ያሉ የእመቤታችን ቅድመ አያቶቿ ጴጥሪቃ ቴክታ ሲባሉ “ወኮኑ ክልኤሆሙ ጻድቃን ወፈራህያነ እግዚአብሔር ወይትአመንዎ ለአምላኮሙ በጥቡዕ ልብ እንበለ ኑፋቄ” ይላል (ኹለቱም ሰዎች ደጋጐችና እግዚአብሔርን የሚፈሩ ያለምንም መጠራጠር በፍጹም ልቡናቸው በአምላካቸው የሚተማመኑ ነበሩ)።

❖ እነርሱም በጊዜው ይኽ ቀራችኊ የማይባሉ ባለጠጎች ነበሩ፤ ከሀብታቸው ብዛት የተነሣ ወርቁን ብሩን እንደ ዋንጫ እያሠሩ በላሙ በበሬው ቀንድ ላይ ይሰኩት ነበር፤ ይኽን ያኽል አቅርንተ ወርቅ፣ አቅርንተ ብሩር እየተባለ ይቈጠር ነበር፤ የዕንቊ ጽዋ እንኳ ፸፣ ፹ ያኽል ነበራቸው ይላል ፡፡

❖ ከዕለታት ባንዳቸው ጴጥሪቃ ወደ ቤተ መዛግብቱ ገብቶ የሀብቱን ብዛት አይቶ ሚስቱ ቴክታን “ለመኑ ዘዘገብነ መዛግብቲነ አልብነ ውሉድ ዘይወርሰነ አንቲኒ ወአነሂ መካን ንሕነ” (የሰበሰብነው ገንዘብ ስንኳን ለኛ ለልጅ ልጅ ይተርፍ ነበር አንቺም እኔም መካኖች ነንና የሚወርሰን ልጅ የለንም) በማለት ተናገራት፤ ርሷም እንዲኽ ማለቱ ወላድ የፈለገ መስሏት በሐዘን ኾና “አምላከ እስራኤል ከኔ ልጅ ባይሰጥኽ ከሌላ ይሰጥኽ ይኾናልና ሌላ አግብተኽ ውለድ” አለችው።

❖ ርሱም “አነሂ ኢይፈቅድ የአምር አምላከ እስራኤል ከመ ኢየሐስቦ ለልብየ” (ይኽንስ እንዳላደርገው በልቤም እንዳላስበው የእስራኤል አምላክ ያውቃል) በማለት ተናገረ፡፡ ርሷም ዐዝና ሳለ ራእይ ታያለች፤ ነጭ እንቦሳ ከማሕፀኗ ስትወጣ እንቦሳዪቱ እንቦሳ እየወለደች እስከ ሰባት ስትደርስ ሰባተኛዋ ጨረቃን ስትወልድ፤ ጨረቃ ፀሓይን ስትወልድ አየች።

💥 በአድናቆት ለባሏ “ግሩም ግብሩ ለእግዚአብሔር ትማልም ርኢኩ በሕልምየ ጸዐዳ ጣዕዋ ወጽአት እምከርሥየ ይእቲኒ ወለደት ጸዐዳ ጣዕዋ እስከ ሰብዐቲሆን ወሳብዕታኒ ወለደት ወርኀ ወወርኅኒ ወለደት ፀሓየ” (የእግዚአብሔር ሥራው ድንቅ ነው፤ ትናንትና ማታ በሕልሜ ነጭ ጥጃ ከማሕፀኔ ስትወጣ ያችም ነጭ ጥጃ ደግሞ ነጭ ጥጃ ስትወልድ እንደዚኽ እየኾነ እስከ ሰባት ትውልድ ሲደርሱ ሰባተኛዪቷም ጨረቃን ስትወልድ ጨረቃዋ ደግሞ ፀሓይን ስትወልድ አየኊ) በማለት አስረዳችው።

❖ ርሱም በእጅጉ ተደንቆ ሕልም ወደሚፈታ ሰው ዘንድ በመኼድ የሚስቱን ራእይ ነገረው፤ ያም ሕልም ተርጓሚ ምስጢር ተገልጾለት ሰባት አንስት ጥጆች መውለዳችኊ ሰባት ሴቶች ልጆች ይወለዳሉ፤ ነጭ መኾናቸው ደጋጎች ልጆች መኾናቸው ሲኾን “ወሳብእታኒ ትከብር እመላእክት ወትትሌዐል እምኲሉ ሰብእ ወበእንተ ፀሓይኒ ኢያእመርኩ” (ሰባተኛዪቱ ጨረቃን መውለዷ ከሰው የበለጠች ከመላእክት የከበረች ናት፤ የፀሓይ ነገር ግን አልተገለጸልኝም) በማለት ተረጐመለት፤ ርሱም ለሚስቱ ነገራት፤ ርሷም “የእስራኤል አምላክ የሚያደርገውን ርሱ ያውቃል” በማለት ፈጣሪዋን አመሰገነች፡፡

❖ ከዚያም ፀንሳ ሴት ልጅ ወለደች ስሟንም ሔሜን አሏት፤ ሔሜን → ዴርዴን ወለደች፤ ዴርዴም → ቶናን፤ ቶናም →ሲካርን ወለደች፤ ሲካርም→ ሴትናን፤ ሴትናም →ሔርሜላን ወለደች፤ ሔርሜላም የተከበረችና የተመረጠች ዓለሙን ኹሉ ለፈጠረ ጌታ አያት ለመኾን የበቃች ሐናን ወልዳለች።

💥 የዝማሬና የትንቢት ጸጋ ከእግዚአብሔር የተሰጡት ክቡር ዳዊት ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ክብር በተለይም ስለ ሥርወ ልደቷ አስቀድሞ መንፈስ ቅዱስ ገልጾለት በመዝ ፹፮፥፩‐፯ ላይ “መሠረታቲሃ ውስተ አድባር ቅዱሳን” (መሠረቶቿ በተቀደሱ ተራሮች ላይ ናቸው) በማለት የእመቤታችን ሥርወ ልደት ከቤተ መንግሥት ከቤተ ክህነት ከኾኑት ከተቀደሱት ከቅዱሱ ኢያቄምና ከቅድስቲቱ ሐና የመኾኑን ነገር በምሳሌ የገለጸው።

❖ ሐና በመልካም አስተዳደግ አድጋ አካለ መጠን ስታደርስ ከነገደ ይሁዳ ከመንግሥት ወገን የተወለደ የቅስራ ልጅ የአልዓዛር የልጅ ልጅ ከሚኾን ከኢያቄም ጋራ አስተጫጭተው አጋቧት፡፡ ሐናና ኢያቄምንም “ወክልኤሆሙ ኄራን ወሥሙራን እሙንቱ ወየሐውሩ በሕገ እግዚአብሔር እስመ እግዚአብሔር ኀረዮሙ ወአፍቀሮሙ ትካት” ይላቸዋል።

💥 እግዚአብሔርን የሚወድዱ በሕጉ የሚኖሩ ደጋጎችና አምላክም የመረጣቸው ሲኾኑ ሐና መካን በመኾኗ ምክንያት ኹለቱም ወደ ቤተ እግዚአብሔር ዕለት ዕለት በመኼድ ለዐይናቸው ማረፊያ ለልባቸው ተስፋ የሚኾን ልጅ እንዲሰጣቸው ይለምኑ እንደነበር፤ “Protoevangelium of James” (ፕሮቶቫንጊሊዩም ኦፍ ጀምስ) የሚለው ያዕቆብ የጻፈው ጥንታዊዉ መጽሐፍ በስፋት ይገልጻል፡፡

❖ ከዕለታት ባንደኛው ሲያዝኑ ሲጸልዩ ውለው ሲመለሱ “ወርእዩ አርጋበ እንዘ ይትፌሥሑ ምስለ ውሉዶሙ” ይላል ርግቦች ከልጆቻቸው ጋር ደስ ብሏቸው ሲጫወቱ አይተው ሐና “አቤቱ ጌታዬ ግዕዛን ለሌላት እንስሳ ልጅ የሰጠኽ አምላክ ምነው ለኔ ልጅ ነሣኸኝ” ብላ ምርር ብላ አለቀሰች፤ ወዲያው ሱባዔ ይገባሉ፤ ኢያቄም ወደ በረሓ ኼዶ ሲጸልይ ሐና ደግሞ በቤቷ ዙሪያ ባለው የተክል ቦታ ሱባዔ ያዘች፤ በሱባዔያቸው ፍጻሜ ኹለቱም ራእይ አይተው ተነጋግረዋል፡፡

❖ “ይቤላ ኢያቄም ለሐና ብእሲቱ እንዘ ይትረኀዉ ሰብዐቱ ሰማያት ዖፍ ጸዐዳ መጽአ ኀቤየ ወነበረ ዲበ ርእስየ” ይላል ሰባቱ ሰማያት እንደ መጋረጃ ተገልጠው ከላይኛው ሰማይ ነጭ ዎፍ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየኊ ብሎ የተገለጸለትን ለሐና ነግሯታል፤ ይኸውም የራእዩ ምስጢር፡- ዎፍ የተባለው አካላዊ ቃል ክርስቶስ ሲኾን፤ ነጭነቱ ንጽሐ ባሕርዩ ነው፤ ከላይ ወርዶ በራሴ ላይ ሲቀመጥ አየኊ ማለቱ የኢያቄምን ባሕርይ ባሕርይ እንደሚያደርግ ሲያጠይቅ ሲኾን፤ ሰባቱ ሰማያት የተባሉ የጌታችን ምልአቱ፣ ስፍሐቱ፣ ርቀቱ፣ ልዕልናው፣ ዕበዩ ናቸው፡፡

❖ ሐናም ተገልጾላት “ትቤሎ ሐና ለኢያቄም ብእሲሃ አነኑ ርኢኩ በሕልምየ ርግብ ጸዐዳ መጽአት ኀቤየ ወነበረት ዲበ ርእስየ ወቦአት ውስተ እዝንየ ወኀደረት ውስተ ከርሥየ” ይላል ለባሏ ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ በዦሮዬ ገብታ በማሕፀኔ ስትተኛ አየኊ ብላዋለች።

👉 ይኽ የራእይ ምስጢር፡- ርግብ የተባለች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስትኾን፤ ነጭነቷ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ዘላለማዊ ድንግልናዋ ነው፤ ነጭ ርግብ መጥታ በራሴ ላይ ተቀምጣ ከራሴ ላይ ወርዳ ወደ ዦሮዬ ገብታ በማሕፀኔ ስትተኛ አየኊ ማለቷ ብሥራተ ገብርኤልን በዦሮዋ ሰምታ በግብረ መንፈስ ቅዱስ አምላክን የምትፀንሰውን ንጽሕት ርግብ የተባለችውን እመቤታችንን የምትወልድ መኾኗን ሲያጠይቅ ነው፡፡

❖ ኢያቄምና ሐናም ይኽነን ራእይ ሐምሌ ፴ ቀን ካዩ በኋላ “ወንድ ልጅ ብንወልድ ወጥቶ ወርዶ ይርዳን አንልም ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ ይኾናል፤ ሴትም ብንወልድ ለቤተ እግዚአብሔር መጋረጃ ፈትላ ትኑር” ብለው ስእለት ከተሳሉ በኋላ ራእይ አየን ብለው ዕለቱን አልተገናኙም፤ አዳምንና ሔዋንን “ብዙ ተባዙ ምድርንም ምሏት” ብሎ የተናገረው አምላክ ለእኛም ይግለጽልን ብለው ዕለቱን አልጋ ምንጣፍ ለይተው እስከ ሰባት ቀን ድረስ እየብቻቸው ሰነበቱ።

❖ ነሐሴ በባተ በሰባተኛው ቀን “ከሰው የበለጠች ከመላእክት ኹሉ የከበረች ልጅ ትወልዳላችኊ" ብሎ መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል ለሐና ነግሯት በፈቃደ እግዚአብሔር በብሥራተ መልአክ እመቤታችን ነሐሴ ሰባት እሑድ ተፀንሳለች፤ በእናቷ ማሕፀን ሳለችም “መንፈስ ቅዱስ ዐቀባ እምከርሠ እማ” እንዲል እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ጥንተ አብሶ ባመጣው መርገም እንዳትያዝ ጠብቋታል፡፡

❖ ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም መፀነስ ከሊቃውንት መኻከል አባ ጽጌ ድንግልና አባ ገብረ ማርያም ዘደብረ ሐንታ በማሕሌተ ጽጌ መጽሐፋቸው ላይ
“ሚ ቡርክት ወቅድስት ይእቲ
ሰዓተ ትፍሥሕት ሐና ዘጸገየተኪ ባቲ
ወፈረየኪ ለሕይወት ኢያቄም መዋቲ
እሴብሕ ተአምረኪ ርግብየ አሐቲ
ወድኀኒተ ኲሉ ዓለም እስመ ኮንኪ አንቲ”
(ሐና አንቺን የፀነሰችባት የደስታ ቀን ምን ያኽል የተባረከች የተቀደሰች ናት፤ ሟች ኢያቄምም ለሕይወት አንቺን ያፈራባት ቀን ምን ያኽል የተባረከች የተቀደሰች ናት፤ አንዲቱ ርግቤ ማርያም አንቺ የዓለሙ ኹሉ መድኀኒት ኾነሻልና ታምርሽን አመሰግናለኊ) በማለት ዓለምን ኹሉ በደሙ ፈሳሽነት ያዳነ ንጉሣችን፣ ፈጣሪያችን ክርስቶስን በድንቅ ተአምር ማኅተመ ድንግልናዋ ሳይለወጥ የወለደችልን ምክንያተ ድኂን ርግበ ሰሎሞን የተባለች የቅድስት ድንግልን የመፀነሷን ነገር በአድናቆት ገልጸዋል፡፡

❖ ታላቁ ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫም በአርጋኖን መጽሐፉ ላይ የዜና ጽንሰቷን ነገር ሲገልጽ “ወይእዜኒ ኦ ውሉደ እግዚአብሔር ወማኅበረ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናስተብፅዖሙ ለሐና ወለኢያቄም ...” (አኹንም የእግዚአብሔር የጸጋ ልጆችና የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ማኅበሮች ሆይ ይኽቺን የተባረከችና የተመረጠች ሙሽራ የወለዱልንን ኢያቄምንና ሐናን እናመስግናቸው የማትነቀፍ የእስራኤል ድንግልን የተባረከችዋን ፍሬ ያፈራችበትን ንጽሕት የምትኾን የሩካቤያቸው ዕለት እንደምን ያለች ዕለት ናት? ከይሁዳ ወገን ለኾነችው ንጽሕት ርግብ መፀነስ በእግዚአብሔር ፈቃድ የተደረገ የጾታዊ ተዋሕዷቸው ቀን ይኽቺ እንዴት ያለች የተመረጠች ቀን ናት፤ ለንጉሥ ማደሪያ አዳራሽ መመሥረት የተደረገባት (የኾነባት) የደስታ ቀን እንዴት ያላት ቀን ናት?) በማለት የፅንሰቷን ነገር አድንቋል።

❖ ሊቁ አባ ሕርያቆስም በቅዳሴ ማርያም መጽሐፉ በቊ ፴፰ ላይ “ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተፀነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ” (ድንግል ሆይ በኀጢአት ፍትወት የተፀነስሽ አይደለሽም በሕግ በኾነ ሩካቤ ከሐና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጂ) በማለት ቅድስት ድንግል ማርያም ጥንተ ኀጢአት ካመጣው መርገም በፅንሰቷ ጊዜ እንዳትያዝ በመንፈስ ቅዱስ ጸጋ የተጠበቀ መኾኑን ተናግሯል፡፡

❖ “ወእምድኅረ ስድስቱ አውራኅ ተዐውቀ ፅንሳ ለሐና” ይላል፤ ከስድስት ወርም በኋላ የሐና ፅንሷ እየታወቀ ሲመጣ ጎረቤቶቿ መፅነሷን ይረዱ ዘንድ በአድናቆት ማሕፀኗን ይዳስሱ ነበር፤ በተለይም ዐይኗ የታወረ የሐና ዘመዷ የአርሳባን ልጅ የምትኾን አንዲት ሴት የሐናን ማሕፀን ዳስሳ ዐይኗን ብትነካው በርቶላት በታላቅ ደስታ ኾና “ብፅዓን ለኪ ኦ ሐና እስመ እም ፍጥረተ ዓለም አልቦ ዘከማኪ ዘይፌውስ በከርሡ አዕይንተ ዕውራን” (ሐና ሆይ ብፅዓን ይገባሻል ዓለም ከተፈጠረ ዠምሮ እንዳንቺ በማሕፀኑ የዕውራንን ዐይን የሚያበራ የለምና) በማለት አመስግናታለች፤ ከዚኽ በኋላ ዝናዋ በሀገሩ ኹሉ ተሰምቶ ሕሙማን ኹሉ ማሕፀኗን እየዳሰሱ ይፈወሱ ነበር፡፡

❖ አባ ጽጌ ድንግልና አባ ገብረ ማርያም ዘደብረ ሐንታ በማሕሌተ ጽጌ መጽሐፋቸው ላይ ይኽነን ሲገልጹ፦
“ጸግይየ ሣዕረ ዘኪሩቤል ልሳነ
ተአምረኪ በነጊር እመ ኢፈጸምኩ አነ
ባሕቱ አአኲት ማርያም ዘጾረተኪ ማሕፀነ
እንዘ ሀለወት ፀኒሳ ኪያኪ ርጢነ
ለለገሰስዋ ላቲ ትፌውስ ዱያነ”
(ሳርን የኾንኊ እኔ የኪሩቤል አንደበትን ገንዘብ አድርጌ ታምርሽን በመንገር በማስተማር ባልፈጽምም ነገር ግን ማርያም የተሸከመቺሽን ማሕፀን አመሰግናለኊ፤ መድኀኒት አንቺን ፀንሳ ሳለች ርሷን የዳሰሷትን ድዉያንን ኹሉ ትፈውስ ነበር) በማለት እመ መድኅነ ዓለም ገና ሳትወለድ የተሠራውን ድንቅ ተአምር አመስግነዋል፡፡

❖ ይኽ የቅድስት ድንግል ማርያም የፅንሰት በዓል በመላው ዓለም የሚታወቅ ሲኾን ጥንታዊት፣ ሐዋርያዊት የኾነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን የአምላክ እናት የተፀነሰችበት ይኽነን በዓል ነሐሴ ፯ ቀን በታላቅ ድምቀት በማሕሌት፣ በቅዳሴ የምታስበው ሲኾን በዓሉም “ፅንሰታ ለማርያም” በመባል ይታወቃል፤ በዓለም ላይ ያሉ ክርስቲያኖች ደግሞ በዓሉን “The conception of the Theotokos” (የአምላክ እናት መፀነስ) በማለት ሲያከብሩት ወሩን ግን የልደት በዓልን ለማክበር በሚዘጋጁበት በታኅሣሥ አድርገው በ፱ኛው ቀን “December 9” ላይ ያስቡታል፡፡
✍ (ነገረ ማርያም በሐዲስ ኪዳን ከሚለው መጽሐፌ የተወሰደ፤ በመጋቤ ሐዲስ ዶክተር ሮዳስ ታደሰ የታተመ)
[የአምላክ እናት ሆይ እንወድሻለን]
❖መልካም በዓል❖

Address

Oromia Region

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when ንዋየ ወርቅ-Newaye werqe posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Videos

Share

Category