13/12/2025
በሀዲያ ዞን የወጣቶችን ሥራ አጥነት ችግር ለመፍታት ትኩረት ተሰጥቶ እየተሠራ ነው።
በዞኑ የወጣቶች ሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትኩረት አድርጎ የሚሠራ (YNSD) Youth Network for Sustainable Development የተሰኘ መንግሥታዊ ያልሆነ ግብረ ሰናይ ድርጅት ከባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር መድረክ በሆሳዕና ከተማ አካሂዷል።
ሆሳዕና፣ታህሳስ 04/2018 ዓ.ም(ሀዲያ ዞን ኮሙኒኬሽን )
በሀዲያ ዞን ከሚገኙ መዋቅሮች በሆሳዕና ከተማ አስተዳደር፣በሶሮ ፣ በሌሞ እና በሻሾጎ ወረዳዎች የወጣቶች ሥራ ዕድል ፈጠራ ላይ ትኩረት አድርጎ የሚሠራ (YNSD) Youth Network for Sustainable Developmet የተሰኘ መንግሥታዊ ያልሆነ ግብረ ሰናይ ድርጅት ከባለድርሻ አካላት ጋር የምክክር መድረክ አካሂዷል።
ድርጅቱም ከማስተር ካርድ ፋውንዴሽን እና ፍቅር በሕይወት ከተሰኙ ማህበራዊ ድርጅቶች ጋር በመተባበር በወጣቶች ሥራ ዕድል ፈጠራ፣ በወጣቶች አመለካከት፣ ሥነምግባርና በሌሎችም ጉዳዮች ዙሪያ የምክክርና የልምድ ልውውጥ መድረክ አካሂዷል።
በምክክር መድረኩም የሀዲያ ዞን ዋና አስተዳደርን ወክለው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የሀዲያ ዞን አስተዳደር ጽህፈት ቤት ኃላፊ የዕለቱ ክብር እንግዳ አቶ ታገሠ ዶባሞ በዚህ ወቅት እንደገለፁት ይህ (YNSD) Youth Network for Sustainable Developmet የተሰኘ መንግሥታዊ ያልሆነ ግብረ ሰናይ ድርጅት ከማስተር ካርድ ፋውንዴሽን እና ፍቅር በሕይወት ከተሰኘው ማህበራዊ ድርጅት ጋር በመተባበር በዞኑ ከሚገኙ መዋቅሮች በሶስት ወረዳና ሆሳዕና ከተማ አስተዳደር በርካታ ተግባራትን እያከናወነ መቆየቱን አንስተዋል።
ድርጅቱ በወጣቶች መሪነት ፣ በሥራ ፈጠራ እና በአመለካከት ዙሪያ ለሴቶች ለወጣቶች እና ተጋላጭ በሆኑ አካላት ላይ አፅንኦት ሰጥቶ እየሰራ መቆየቱንም ገልጸዋል።
በዚህም ወጣቶቹ በማህበረሰብ ውስጥ ገብተው የአረጋውያን ቤት ከማደስና ድልድይና መንገድ ጥገናን ጨምሮ በርካታ የማህበረሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የመሠረተ ልማት ሥራዎችን መከናቸውን አብራርተዋል ።
አቶ ታገሠ አክላውም ድርጅቱ በይበልጥ ሴቶችን(70%)፣ተጋላጭ ማህበረሰብ ክፍሎች/ የአካል ጉዳተኞች(10%) እና ወጣቶችን(20%) በድምሩ ለአንድ ሺህ 500 ወጣቶችን ተጠቃሚ ለማድረግ አጽንኦት ሰጥቶ የሚሠራ ድርጅት መሆኑን አንስተው
ተግባሩም ይበልጥ ውጤታማ መሆን እንዲችል ዞኑ ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ እንደሚገኝም አስረድተዋል።
የሀዲያ ዞን የሥራ ዕድል ፈጠራና ኢንተርፕራይዞች ልማት መምሪያ ምክትል ኃላፊ ሞርካ ሞግሶ(ዶ/ር) በበኩላቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመራ ከመጣው አዳጊ የህዝብ ፍላጎቶች አንፃር መንግስት ብቻውን ማሟላት አዳጋች እንደሆነ አንስተው፣
መንግስታዊ ያልሆኑ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች በመንግስት ያልተሸፈኑ የልማት ፍላጎቶችን በማሟላት የህዝብን ተጠቃሚነት ለማረጋገጥ ያላቸው ሚና ከፍተኛ ነው ብለዋል።
በዚህም (YNSD) Youth Network for Sustainable Development የተሰኘ መንግሥታዊ ያልሆነ ግብረ ሰናይ ድርጅት ከማስተር ካርድ ፋውንዴሽን እና ፍቅር በሕይወት ከተሰኙ ማህበራዊ ድርጅቶች ጋር በመተባበር በዞኑ አራት መዋቅሮች በወጣቶች ዙሪያ እየሠራ ያለው ጅምር ሥራ አበረታች መሆኑን አመላክተዋል።
በተሠራው ሥራም ውጤቶች መመዝገባቸውን የጠቆሙት ኃላፊው ድርጅቱ ያመቻቸውን የብድር አማራጮች በመጠቀም ወጣቶች ቀጣይነት ያለውን የሕይወት ለውጥ ለማምጣት በሚደረገው ርብርብ በየደረጃው ያሉ የመንግሥት የሥራ ኃላፊዎችና የሥራ ዕድል ፈጠራ ተቋማት ኃላፊነታቸውን በአግባቡ እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል ።
የCommunity Service As a Pathway to work (CSPW) የግብረ ሰናይ ድርጂት ሶዶ ክላስተር አስተባባሪ አቶ ኢያሱ ስዩም ለተሳተፊዎቹ ባደረጉት ገለፃ፣ፕሮጀክቱ የሶዶ ክላስተርን ማዕከል አድርጎ በደቡብ ኢትዮጵያ እና በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በወጣቶች ዙሪያ በርካታ ሥራዎች እየተሠሩ መቆየታቸውን አስገንዝበዋል።
በሀዲያ ዞንም ከሚገኙ መዋቅሮች ሆሳዕና ከተማ፣ ሌሞ ወረዳ፣ ሻሾጎ ወረዳ እንዲሁም የሶሮ ወረዳን ጨምሮ ዘርፈብዙ ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል ።
አቶ ኢያሱ ስዩም አክላውም በባለፉት የሥራ ወቅቶች በሶስቱ ወረዳዎችና በሆሳዕና ከተማ አስተዳደር በወጣቶች መሪነት ሚና ፣ በሥራ ፈጠራ እና በአመለካከት ዙሪያ ሰፊ ሥራዎች ተሰርተዋል።
ከተሳታፊዎቹ መካከል የሀዲያ ዞን ሴቶችና ህፃናት ጉዳይ መምሪያ ምክትል ኃላፊ ወይዘሮ ዓለምፀሐይ ተሰማ እና የሻሾጎ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ግርማ ሎቤ በየበኩላቸው በሰጡት አስተያየት ፣ድርጅቱ በዞኑ የጀመራቸው ሥራዎች ቀድሞውኑ በሰው ተኮር መንግስታችን ትኩረት የተሰጠባቸው ናቸው በማለት
ሁሉንም ወጣት በማሳተፍ ሥራውን ውጤተማ ለማድረግ የበኩላቸውን ድርሻ ለመወጣት ዝግጁ መሆናቸውን ገልፀዋል።
በመጨረሻም የምክክር መድረኩ በሀዲያ ዞን ወጣቶችና ስፖርት መምሪያ ኃላፊ አቶ ተምሬ ኤርሚያስ ቀጣይ የሥራ መመሪያና ማጠቃለያ ሀሳብ ተሰጥቶ ተጠናቋል።
በንጉሤ ዶሌቦ