31/12/2025
🇮🇷በኢራን በኑሮ ውድነት የሙላዎችን አገዛዝ የሚቃወሙ ተቃውሞዎች እየተጠናከሩ ነው
በኢራን የሙላዎችን አገዛዝ የሚቃወሙ ተቃውሞዎች ቁጥራቸው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ መጥቷል። የሪያል የመግዛት አቅም በከፍተኛ ሁኔታ መቀነሱን ተከትሎ ነጋዴዎችን እና በሺዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎች ተቃውሞውቸው በስፋት እየተሰራጨ ይገኛል።
ተቃዋሚዎቹ ነፃነትን፣ የገንዘብ ድጋፍን እና የሙላዎች ሥርዓት እንዲወገድ እየጠየቁ ነው።
በኢራን የሚካሄደው የፀረ-ሙላዎች ተቃውሞ ለሦስት ተከታታይ ቀናት የቀጠለ ሲሆን፣ መጠኑም እየሰፋ መጥቷል። የሀገሪቱ ገንዘብ ሪያል ዋጋ በከፍተኛ ሁኔታ በመውረዱ እና ከእስራኤል ጋር ባለው ግጭት ምክንያት ተባብሶ በቀጠለው የኢኮኖሚ ቀውስ ሳቢያ ነጋዴዎች እና ወደ አደባባይ ወጥተዋል። የኢንተርኔት መድረኮች እና በስደት ላይ ያሉ ወገኖች እንደሚሉት አሁን ላይ በሺዎች የሚቆጠሩ ተማሪዎች ተቃውሞውን ተቀላቅለዋል።
የገንዘብ ምንዛሬ ውድቀት እና የኢኮኖሚ ጥፋት
ሁሉም ነገር የጀመረው ባለፈው እሁድ የሪያል ዋጋ በታሪክ ዝቅተኛው ደረጃ ላይ መድረሱን ተከትሎ ነው። በዋጋ ግሽበት እና በማዕቀብ ምክንያት የኢራን ሪያል ዋጋ ከ2025 መጀመሪያ ጀምሮ በከፍተኛ ሁኔታ የቀነሰ ሲሆን፣ ከአሜሪካ ዶላር ጋር ሲነጻጸርም ዝቅተኛው ደረጃ ላይ ደርሷል።
በጥቁር ገበያ ያለው የሪያል ምንዛሬ ዋጋ ማዕከላዊ ባንኩ ከሚያወጣው ይፋዊ ተመን በእጅጉ የላቀ ነው።
የምግብ እና የገቢ ዕቃዎች ዋጋ ሰማይ እየነካ ሲሆን፣ መካከለኛውን የህብረተሰብ ክፍል ክፉኛ እየጎዳው ይገኛል። በቴህራን፣ ኢስፋሃን፣ ሺራዝ እና ሌሎች ከተሞች የሚገኙ ነጋዴዎች በባዛሮች ውስጥ የሥራ ማቆም አድማ በማድረግ የመንግሥትን ፖሊሲዎች ተቃውመዋል። ይህ ቀውስ በማዕቀብ፣ በሙስና እና በከፍተኛ ወታደራዊ ወጪ ምክንያት የመጣ መሆኑ ይነገራል።
በቴህራን፣ ኢስፋሃን፣ ያዝድ እና ዛንጃን የሚገኙ ታዋቂ ተቋማትን ጨምሮ እስከ አሥር የሚደርሱ ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎች ተቃውሞውን ተቀላቅለዋል። በግቢዎች ውስጥ "ለአምባገነኑ ሞት ይሁን፣" "ጋዛም ሆነ ሊባኖስ አያስፈልጉንም - ሕይወቴ ለኢራን ነው" እና "ነፃነት፣ እኩልነት፣ የእስላማዊ ሪፐብሊክ ፍጻሜ ይሁን" የሚሉ መፈክሮች አስተጋብተዋል።
ወጣት ተቃዋሚዎቹ የኢኮኖሚ ድጋፍ ብቻ ሳይሆን መሠረታዊ ነፃነትን እና የሥርዓት ለውጥን እየጠየቁ ነው። በማህበራዊ ሚዲያ ላይ የሚለቀቁ ቪዲዮዎች በዩኒቨርሲቲ ህንጻዎች ፊት ለፊት የተሰበሰቡ ሰፊ ህዝቦችን ያሳያሉ።
የጸጥታ ኃይሎች በአስለቃሽ ጭስ፣ በጎማ ጥይት እና በጅምላ እስራት ምላሽ ሰጥተዋል። በቴህራን እና ኢስፋሃን የጎዳና ላይ ግጭቶች የተከሰቱ ሲሆን፣ የመቁሰል አደጋዎች መድረሳቸውም ተገልጿል።
ተቃውሞው አሁን ወደ ሌሎች ዘርፎች ለምሳሌ ወደ ፋብሪካዎች እየተስፋፋ መሆኑ ተጠቁሟል።
የ71 አመቱ ፕሬዚዳንት ማሱድ ፔዜሽኪያንሁኔታውን ለማረጋጋት ከተቃዋሚዎች ጋር ለመነጋገር ሐሳብ አቅርበዋል። በሕመም ላይ የሚገኙት የ86 አመቱ መንፈሳዊው መሪው አያቶላ አሊ ኻሜኒ እስካሁን ዝምታን መርጠዋል።
የባዛር ነጋዴው መካከለኛ ክፍል እና የፅንፈኛ ተማሪዎች ጥምረት ከ2022ቱ የጅምላ ተቃውሞ በኋላ በገዢው ሥርዓት ላይ የተነሳ ትልቁ አመጽ ተደርጎ ተወስዷል።
መንግሥትን የሚደግፈው "ቴህራን ታይምስ"በድረ-ገጹ
ይህን አስፍሯል;
"ተቃውሞዎች ስለ ወደፊታቸው በሚቆረቆሩና በሂደቱም ላይ ተጽዕኖ ማሳደር እንችላለን ብለው በሚያምኑ ዜጎች በሚኖሩበት በማንኛውም ማህበረሰብ ውስጥ ተፈጥሯዊና መሰረታዊ አካላት ናቸው። ተቃውሞዎች የሥርዓት ውድቀት ምልክቶች ሳይሆኑ፣ የሲቪክ ጤናማነት እንዲሁም የመናገር፣ የመሰብሰብና የመደራጀት ነፃነት መገለጫዎች ናቸው። ለምዕራባውያን አገራት፣ ለሚዲያዎቻቸውና ለፖለቲከኞቻቸው ይህ ሁሉ እውነት ነው—ተቃውሞዎቹ በኢራን ውስጥ ሲካሄዱ ግን ይህ ነገር ሌላ ትርጉም ይሰጠዋል።"