
11/04/2025
" የተፈጠረውን የፖለቲካ ልዩነት በማጥበብ የትግራይን ህዝብ ቀጣይ እጣ ፈንታ ማቃናት ይገባል " - ጄነራል ታደሰ ወረደ
➡️ " ጊዜያዊ አስተዳደሩ ነፃነቱን ጠብቆ ስራውን አንዲሰራ የበኩሌን አስተዋፅኦ እወጣለሁ " - ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል (ዶ/ር) የሚመሩት ህወሓት
በደብረፅዮን ገ/ሚካኤል (ዶ/ር) የሚመራው ህወሓት ፤ " የጊዜያዊ አስተዳደሩ ተቋማዊ ነፃነቱን ጠብቆ ስራውን አንዲሰራ የበኩሌን አስተዋፅኦ እወጣለሁ " አለ።
የአዲሱ የትግራይ ጊዚያዊ አስተዳደር ፕሬዜዳንት ሌተናል ጀነራል ታደሰ ወረደ በይፋ ስራቸውን የጀመሩ ሲሆን ከነባሩ ካቢኔና ከደብረፅዮን (ዶ/ር) ህወሓት ጋር ተገናኝተዋል።
ካቤኔያቸው መልሰው እንደሚያደራጁ የገለፁት ፕሬዜዳንቱ ጎን ለጎን የሦስት ወር እቅድ እንዲዘጋጅ አዘዋል።
የስራቸው ዋና ማጠንጠኛ የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት ሙሉ ለሙሉ መተግበር መሆኑ ገልጸዋል።
- የህዝብ ሰላምና ደህንነት በአስተማማኝነት መጠበቅ
- የክልሉ ኢኮኖሚ ማነቃቃት
- የአስተዳደር መዋቅሩን ማስተካከል የትኩረት አቅጣዎች መሆናቸው ተናግረዋል።
የተፈጠረውን የፓለቲካ ልዩነት በማጥበብ የትግራይ ህዝብ ቀጣይ እጣ ፈንታ ማቃናት እንደሚገባ ያሳሰቡት ጄነራል ታደሰ " አሸናፊና ተሸናፊ ከሚል መገፋፋት በመውጣት በአብሮነት በመደጋገፍ በጋራ መስራት አለብን " ብለዋል።
" ህወሓትና ጊዚያዊ አስተዳደር " የሚል ልዩነት የሚያሰፋ አጀንዳ እንዲፈታና እንዲዘጋ እንደሚሰሩ ገልጸዋል።
በቅርብ ጊዜ የህዝብ ኮንፈረንስ በማካሄድ ያሉትን ችግሮች ለመፍታት እንዳቀዱና እቅዳቸው እውን እንዲሆን የሁሉም ፓለቲካ ፓርቲዎች ድጋፍ እንደሚሹ ጠይቀዋል።
በተያያዘ ፕሬዜዳንቱ ትላንት ማምሻውን ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል (ዶ/ር) የሚመሩት ህወሓት በፅህፈት ቤቱ ይፋዊ አቀባበል አድርጎላቸዋል።
የፓርቲው ሊቀመንበር ደብረፅዮን ገ/ሚካኤል (ዶ/ር) በአቀባበል ስነ-ስርዓቱ ለፕሬዜዳንቱ ያላቸው መልካም ምኞት በማስቀደም ፤ ጊዚያዊ አስተዳደሩ ተልእኮዎቹ ለመፈፀም በሚያደርገው ጥረትና እንቅስቃሴ የህወሓት ድጋፍ አይለየውም ብለዋል።
" የክልሉና የህዝቡ ችግሮች መፍታት የጋራ አጀንዳ ነው " ያሉት ጄነራል ታደሰ የፓርቲው አመራሮች ላደረጉላቸው አቀባበልና ለገለፁላቸው መልካም ምኞች አመስግነዋል።
" የትግራይና ህዝቡን መልካም ገፅታ ለመመለስ በጋራ ከመስራት ውጪ ሌላ አማራጭ የለም " ሲሉም ተናግረዋል።
መረጃው ከክልሉ ፕሬዝዳንት ፅ/ቤት እና ከህወሓት የማህበራዊ የትስስር ገፅ የተወሰደ ነው።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
መቐለ
ፎቶ፦ TPLF