21/08/2024
የአዲስ አበባ ሁለተኛው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት “በከተማዋ መግቢያ” ቦታዎች ሊከናውን ነው
| የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሁለተኛውን ምዕራፍ የኮሪደር ልማት እንደ ኮዬ አደባባይ፣ ጎሮ እና ሰሚት ባሉ “የከተማዋ መግቢያ” እና “ማስፋፊያ ላይ በሚገኙ” አካባቢዎች ሊያከናውን ነው።
43 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ሁለተኛው ምዕራፍ ግንባታ፤ ከሸገር ከተማ የኮሪደር ልማት ጋር “በማስተሳሰር” እንደሚከናወን ታቅዷል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር “የኮሪደር ልማት” ሲል የጠራውን ዋና ዋና መንገዶችን የማስዋብ፣ የእግረኛ መንገድን የማስፋት፣ መዝናኛ ቦታዎችን የመገንባት እንዲሁም የመንገድ ዳር መብራት እና ቴሌኮሚዩኒኬሽን መስመሮችን በዘመናዊ መንገድ የመዘርጋት ሥራ የጀመረው በዚህ ዓመት የካቲት ወር ላይ ነበር።
የከተማዋን ታዋቂ እና ነባር አከባቢዎችን የሸፈነው የመጀመሪያው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት፤ አምስት መስመሮችን የያዘ ነው። በመጀመሪያው ምዕራፍ ግንባታ ከተከናወነባቸው አካባቢዎች መካከል ፒያሳ፣ አራት ኪሎ፣ ቦሌ፣ መገናኛ፣ ሜክሲኮ እና ሲኤምሲ ይገኙበታል።
የኮሪደር ልማቱ ሲከናወን ተለይም በፒያሳ አካባቢው ጥንታዊ ኪነ ሕንጻዎችን ጨምሮ በርካታ ቤቶች የፈረሱ ሲሆን፣ በዚሁ ግንባታ ምክንያት 11 ሺህ ገደማ ነዋሪዎች ከአካባቢው መነሳታቸውን ከንቲባዋ አስታውቀው ነበር።
የከተማ አስተዳደሩ፤ በድምሩ 48 ኪሎ ሜትር ለሚሸፍነው ለመጀመሪያው ዙር የኮሪደር ልማት፤ 33 ቢሊዮን ብር ወጪ ማድረጉንም መግለጻቸውም ይታወሳል።
በጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ግምማ እየተደረገበት የተካሄደው ይህ የኮሪደር ልማት፤ የአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤን ጨምሮ የከተማዋ ከፍተኛ ባለሥልጣናት መስመሮችን ተከፋፍለው ሥራውን መርተውታል።
ከኮሪደር ልማቱ መስመሮች ውስጥ ቀድሞ የተመረቀረው በከንቲባዋ ክትትል ስር የነበረው ከአራት ኪሎ ፒያሳ የሚደርሰው መንድ ሲሆን፣ ባለፈው ሳምንት ሰኞ የተመረቀውን ከመገናኛ ሲኤምሲ የተዘረጋውን ልማት ጨምሮ ሌሎቹ መስመሮች በተለያዩ ጊዜያት ክፍት ሆነዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፤ በመጀመሪያው ምዕራፍ የገነባቸውን እነዚህን “መሃል ከተማ” ውስጥ የሚገኙ መስመሮች፤ “የከተማዋ መግቢያ ተብለው የተለዩ ቦታዎች እና በማስፋፊያ ከሚገኙ አካባቢዎች ጋር ለማስተሳሰር” ማቀዱን ቢቢሲ ከከተማ አስተዳደሩ ጥናት ተመልክቷል።
በምዕራፍ ሁለት የሚከናወኑ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ላይ የተደረገው ይህ ጥናት በከተማዋ የፕላን እና ልማት ቢሮ የተዘጋጀ ነው። በአጠቃላይ 43 ኪሎ ሜትር ርዝመት የሚኖረው የምዕራፍ ሁለት የኮሪደር ልማት፤ ቦሌ፣ ለሚ ኩራ እና አቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተሞችን እንደሚያካትት የጥናት ሰነዱ ያሳያል።
ሁለተኛው ምዕራፍ ግንባታ በአምስት መስመሮች ላይ የሚከናወን ነው። ከእነዚህ መስመሮች ውስጥ ከፍተኛ ዝርመት ያለው “ከአንበሳ ጋራዥ - መብራት ኃይል - ጎሮ - ኮዬ አደባባይ” የሚደርሰው መንገድ ነው። ይህ መስመር 14.8 ኪሎ ሜትር የሚሸፍን ነው።
“ከቦሌ ካርጎ - ቡልቡላ - ኮዬ አደባባይ” የሚደርሰው ሁለተኛው ረጅም መስመር ደግሞ 12.8 ኪሎ ሜትር ርዝመት አለው። በሁለተኛው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት ውስጥ የተካተተው ሌላኛው መስመር “ከቦሌ ድልድይ” ተነስቶ “በቦሌ ሆምስ - በአየር መንገድ ቪአይፒ መግቢያ” አድርጎ መዳረሻው “ጎሮ” አካባቢ ነው።
“ከጎሮ አደባባይ” የሚነሳው አራተኛው መስመር አምስት ኪሎ ሜትር ርዝመት እንደሚኖረው በጥናት ሰነዱ ላይ ሰፍሯል። ይህ መስመር “ከጎሮ አደባባይ - በሰባ ሁለት አካባቢ - ሰሚት ለስላሳ ፋብሪካ አካባቢ - ፍየል ቤት - ሲ ኤም ሲ አደባባይ” አካባቢዎችን ይሸፍናል።
“ከፍየል ቤት - ፊጋ - ሰሃሊተ ምህረት አደባባይ - ጃክሮስ” የሚደርሰው አምስተኛው መስመር ደግሞ 5.9 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው ነው።
በከተማዋ የአስተዳደር ወሰን ማብቂያ አካባቢ የሚገኙ አካባቢዎችን ያካተተው ሁለተኛው ምዕራፍ ግንባታ፤ “በትግበራ ላይ ከሚገኙ የሸገር [ከተማ] ልማት ኮሪደሮች ጋር በማስተሳሰር የሚከናወን” እንደሆነ የጥናት ሰነዱ ያመለክታል።
በአዲስ አበባ ዙሪያ የሚገኙ አምስት ከተሞችን በአንድ የከተማ አስተዳደር ስር በማድረግ ባለፈው ዓመት የተመሠረተው የሸገር ከተማ፤ ባለፈው ሰኔ ወር ላይ “ዘጠኝ የልማት ኮሪደሮችን” በመለየት ወደ ሥራ ለመግባት በዝግጅት ላይ መሆኑን አስታውቆ ነበር።
የአዲስ አበባ ከተማ ፕላን እና ልማት ቢሮ ያዘጋጀው የጥናት ሰነድ፤ ከኦሮሚያ ክልል ሸገር ከተማ ጋር በሚዋሰኑ አካባቢዎች የሚገኙ የኮሪደር ልማት ሥራዎች ከአጎራባቹ ከተማ ጋር “ወጥ የሆነ ዲዛይን ተዘጋጅቶላቸው በጋራ የሚለሙበትን ማዕቀፍ መፍጠር” እንደሚያስፈልግ አስፍሯል።
በሁለተኛው ምዕራፍ ውስጥ የተካተቱ አካባቢዎች ላይ የሚከናወነው የኮሪደር ልማት እንደ መጀመሪያው ምዕራፍ ሁሉ የእግረኛ መንገድን የማስፋት ውጥን ያለው ነው። በዋና መንገድ (አስፓልት) ጠርዝ የሚገኙ አካባቢዎች የአስር ሜትር ስፋት እንዲኖራቸው እንደታሰበ በጥናቱ ላይ ሰፍሯል።
አምስት ሜትሩ የሚውለው ለእግረኛ መንገድ ሲሆን፤ የሳይክል መስመር ደግሞ ሦስት ሜትር ስፋት ይኖረዋል። በአስፓልቱ በኩል የሚኖረው ቀሪው ሁለት ሜትር የአረንጓዴ ልማት ቦታ እንደሚኖረው ጥናቱ ያስረዳunication
የምስሉ መግለጫ,ቦሌ ክፍለ ከተማ አመራሮች በሁለተኛው ምዕራፍ የኮሪደር ግንባታ እየተከናወኑ ያሉ ሥራዎችን ሰኞ ዕለት መጎብኘታቸውን የክፍለ ከተማው ኮሚዩኒኬሽን ዘግቦ ነበር
በአምስቱ መስመሮች የሚገነባው የኮሪደር ልማት በሌሎች አካባቢዎች እንደተሠራው ሁሉ፤ የታክሲ ማቆሚያ ቦታዎችን፣ የሕዝብ መፀዳጃ፣ የመዝናኛ ቦታዎች እንዲሁም በከተማ፣ ክፍለ ከተማ እና ወረዳ ደረጃ የሚገነቡ ፓርኮችን እንደሚያካትት ጥናቱ ገልጿል።
የመኖሪያ ቤቶች ግንባታም የዕቅዱ አካል እንደሆነ የሚያመለክተው ጥናቱ፤ “ከቦሌ ሆምስ - አንበሳ ጋራዥ -አይሲቲ ፓርክ” ባለው አካባቢ ውስጥ “የማስፈሪያ ቦታ” (relocation site) ይኖራል። በዚህ ስፍራ ላይ “ቅይጥ የመኖሪያ ቤቶች” (mixed residence) ይገነባሉ ተብሏል።
በኮሪደር ልማቱ ምክንያት “ሙሉ በሙሉ የሚነሱ” ቦታዎች ጉዳይ በሰነዱ ላይ “ውሳኔ” እንዲሰጥባቸው ከተዘረዘሩ ነጥቦች መካከል ነው። ነባር ግንባታዎች “በልማቱ ውስጥ የሚካተቱበት መንገድ” መፈጠር እንዳለበት የሚያስገነዝበው ሰነዱ፤ ኮሪደር ልማቱ በሚከናወንባቸው መስመሮች ላይ ለሚገኙ ሕንጻዎች ሁለት አማራጮችን አካትቷል።
“ከሁለት ወለል በላይ” ላላቸው ሕንጻዎቸ የተቀመጠው አማራጭ “ታዛ (Arcade) እንዲያካትቱ ማድረግ” የሚል ነው። ይህ ዓይነቱ አማራጭ በመጀመሪያው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት ላይ በሚገኙ ሕንጻዎች ላይ የተተገበረ ሲሆን፣ ሕንጻዎች የምድር ወለላቸውን የፊት ለፊት ገጽታ በማፍረስ ለእግረኛ ክፍት አድርገዋል።
ከሁለት ወለል በታች ላሉ ግንባታዎች የተቀመጠው አማራጭ “በጥናቱ መሠረት ወደ ልማት ውስጥ ማስገባት” የሚል ነው። በምዕራፍ ሁለት በተካተቱ ቦታዎች ለሚገኙ “ይዞታዎችን የመለየት፣ የመተንተን፣ ግምት እና የምትክ አገልግሎቶችን የመለየት ሥራ” እየተከናወነ መሆኑን ጥናቱ ይጠቅሳል።
በሁለተኛው ምዕራፍ የኮሪደር ልማት ውስጥ ከተካተቱት መስመሮች ውስጥ በቦሌ ክፍለ ከተማ ውስጥ የሚገኙት ሦስት ግንባታዎች “በቅርቡ” እንደተጀመሩ የቦሌ ክፍለ ከተማ አስተዳደር የኮሚዩኒኬሽን ጽህፈት ቤት ለቢቢሲ አረጋግጧል።
በለሚ ኩራ ከፍለ ከተማ የሚገኙት መስመሮች ላይ ደግሞ ሥራውን ለማስጀመር “ከሕብረተሰቡ ጋር ውይይት እየተደረገ” መሆኑን የክፍለ ከተማው የኮሚዩኒኬሽን ጽህፈት ቤት አስታውቋል።
BBC